የግብፁ ፕሬዝዳንት የወቅቱ የአፍሪካ ህብረት ሊቀመንበር ሆኑ

(ኢሳት ዲሲ–የካቲት 4/2011)የግብፁ ፕሬዚዳንት አል ሲሲ የወቅቱ የአፍሪካ ህብረት ሊቀመንበር ሆነው ተመረጡ፡፡

ላለፉት ሁለት አመታት የአፍሪካ ህብረትን በሊቀመንበርነት ሲመሩ የነበሩት ፕሬዝዳንት ፓል ካጋሜ ሊቀመንበርነታቸውን አስረክበዋል፡፡

አል ሲሲ የአፍሪካ ህብረት ሊቀመንበር በመሆን እስከ ፈረንጆቹ 2020 ይቆያሉ ተብሏል፡፡

ፓል ካጋሜ ባደረጉት ንግግር ለአፍሪካ ሀገራት መንግስታት፣ ተቋማት እና ሌሎች አካላት በቆይታቸው ሲያደርጉላቸው ለነበረው ድጋፍ ምስጋና አቅርበዋል፡፡

አል ሲሲ በበኩላቸው በአፍሪካ የድርድር እና የመከላከል ዲፕሎማሲ ሰላምንና ደህንነትን ለማረጋገጥ ዋነኛ መንገድ ሆነው እንደሚቀጥሉ ገልፀዋል፡፡

የአፍሪካን የነገ ተስፋ እያጨለመ የሚገኘውን ሽብርተኝነትን መከላከል ላይ በትኩረት ሊሰራ እንደሚገባም ነው የተናገሩት፡፡

እንዲሁም በአለም ላይ እየታየ ያለው የአየር ለውጥ ዋነኛ ባለድርሻ ያደጉት ሀገራት በመሆናቸው በአካባቢ ጥበቃ የድርሻቸውን ሊወጡ እንደሚገባ አሳስበዋል፡፡