የግራዚያኒ ሀውልት እንዲፈርስ ውሳኔ ተሰጠ

(ኢሳት ዜና–ሕዳር 1/2010)የጣሊያን ፍርድ ቤት ከ5 ዓመት በፊት የተገነባውን የግራዚያኒ ሀውልት እንዲፈርስ ውሳኔ ሰጠ።

በላዚዮ ክፍለ ግዛት አፊሌ ከተማ የፋሺስቱ ሮዶልፍ ግራዚያኒ መታሰቢያ ሀውልትን በገነቡት የከተማዋ አመራሮች ላይ የእስርና የገንዘብ ቅጣት ውሳኔ ማስተላለፉምም ታወቀ።

ዓለም ዓቀፍ ህብረት ለፍትህ የኢትዮጵያ ጉዳይ ለኢሳት እንዳስታወቀው ይህ የጣሊያን ፍርድ ቤት ውሳኔ ለኢትዮጵያውያን ታላቅ ድል ነው።

ሀውልቱን የገነቡትና የፍርድ ቤት ትዕዛዝ ባለማክበር ክስ የተመሰረተባቸው የአፊሌ ከተማ ከንቲባና ሌሎች አመራሮች ከ6 እስከ 8 ወራት እስራት የተፈረደባቸው ሲሆን የገንዘብ ቅጣትም ተጥሎባቸዋል።

ከ1928 እስከ 1933 እንደ ኢትዮጵያ አቆጣጠር ባለው የ5ዓመቱ የፋሺስት ወረራ 1 ሚሊየን ኢትዮጵያውያን ተገድለዋል።

2ሺህ አብያተክርስቲያናት ተቃጥለዋል። ከግማሽ ሚሊየን በላይ ቤቶች ወድመዋል። 14ሚሊየን የቤት እንስሳት አልቀዋል። በገንዘብ ለመተመን የሚያስቸግሩ የሀገር ቅርሶች ተዘርፈው ተወስደዋል።

ፋሺስት ጣሊያን በኢትዮጵያና ህዝቧ ላይ የሰራው ግፍ በታሪክ ሲታወስ የሚኖር ነው።

ያንን አስከፊ የጭካኔ ተግባር ከፈጸሙት የጣሊያን የጦር መሪዎች አንዶ ሩዶልፍ ግራዚያኒ የሚጠቀስ ነው።

ለዚህ ወንጀለኛ የጦር መሪ በጣሊያን ላዚዮ ግዛት አፊሌ ከተማ ሀውልት መቆሙና የመታሰቢያ ሙዚየም መገንባቱ ኢትዮጵያውያንን ብቻ ሳይሆን ፍትህ ፈላጊ የዓለም ህዝብን ያስቆጣ ድርጊት ሆኗል።

አቶ ኪዳኔ ዓለማየሁ የዓለም ዓቀፍ ለፍትህ የኢትዮጵያ ጉዳይ ስራአስኪያጅ ለኢሳት እንደገለጹት ለግራዚያኒ የቆመውን ሀውልትና የተገነባውን ሙዚየም በተመለከተ በአስቸኳይ እንዲፈርሱ ከፍተኛ የሆነ ዘመቻ ሲደረግ ቆይቷል።

ጉዳዩን በፍርድ ቤት ሲከታተሉ ለነበሩ ተቋማት፣ግለሰቦችና ለመላው ኢትዮጵያውያን ባለፈው ማክሰኞ የጣሊያን ፍርድ ቤት ያስተላለፈው ውሳኔ ታላቅ ድል ሆኖ ተመዝግቧል።

ፍርድ ቤቱ ሀውልቱ እንዲፈርስ ብቻ ሳይሆን በዚህ ግንባታ እጃቸውን ያስገቡና እንዳይፈርስ እንቅፋት የሆኑ የአፊሌ ከተማ አመራሮች ላይ የእስርና የገንዘብ ቅጣት ማስተላለፉ ተሰምቷል።