የጅማ ዩኒቨርስቲ ሙስሊም ተማሪዎች ተቃውሞአቸውን ገለጹ

ጥር ፴ (ሰላሳ) ቀን ፳፻፭ ዓ/ም

ኢሳት ዜና:-ስማቸው እንዳይገለጥ የፈለጉ ተማሪዎች ለኢሳት እንደገለጡት ቁጥራቸው ከ500 የማያንስ ሙስሊም የዩኒቨርስቲው ተማሪዎች በስታደየም አካባቢ በመሰባሰብ     ጥያቄያቸው መልስ እንዲያገኝ ጠይቀዋል።  በደህንነት ሀይሎች ታፍነው የተወሰዱት ተማሪዎች ያሉበትን ሁኔታ ዩኒቨርስቲው  እንዲያሳውቃቸው ተማሪዎች ጥያቄ አቅርበዋል። የዩኒቨርስቲው ባለስልጣናት ዲኑ ለስብሰባ ከአካባቢው በመራቃቸው መልስ ሊሰጡዋቸው እንደማይችሉ ለተማሪዎች ቢነግሩም፣ ተማሪዎቹ ግን በተቃውሞአቸው ገፍተውበታል።

ይህን ዜና እስካጠናከርንበት በኢትዮጵያ ሰአት አቆጣጠር እስከ ምሽቱ 12 ሰአት ድረስ ተማሪዎች አልተበተኑም። የግቢው ፖሊሶች ዙሪያቸውን ከበው መታየታቸውን ተማሪዎች ገልጸዋል። የፌደራል ፖሊስ አባላት በአካባቢው ባይታዩም፣ በማንኛውም ሰአት ይደርሳሉ ብለው እንደሚገምቱ ተማሪዎች ተናግረዋል።

ባለፈው ወር ክርስቲያን ተማሪዎች ያነሱትን ተቃውሞ ተከትሎ 3 ተማሪዎች መባረራቸውንና 20 ተማሪዎች ደግሞ ከባድ ማስጠንቀቂያ እንደተሰጣቸው ለማወቅ ተችሎአል።

ሁለት የጎንደር ዩኒቨርስቲ ተማሪዎች ታፍነው መወሰዳቸውን ተከትሎ የዩኒቨርስቲው ተማሪዎች ተቃውሞ አድርገው እንደነበር ይታወሳል።