የዛላ አንበሳ ድንበር በዜጎች ስምምነት ተከፈተ

(ኢሳት ዲሲ–ነሐሴ 21/2010) ለበርካታ አመታት ሲያወዛግብ የቆየው የዛላ አንበሳ ድንበር በዜጎች ስምምነት መከፈቱ ተሰማ።

ይህንን ተከትሎም የሃይማኖት አባቶችን፣የሃገር ሽማግሌዎችን፣ሴቶችንና ወጣቶችን ያካተተ ቡድን በኤርትራዋ የንግድ ከተማ ሰናፌ ወደ ምትገኘው ሰርሃ ከተማ መጓዙ ተሰምቷል።

40 አባላትን አካቷል የተባለው ቡድን ከዛላአንበሳ አለፍ ብላ ወደ ምትገኘው ሰርሃ ከተማ ሲገባም በኤርትራ ወታደሮች አቀባበል ተደርጎለታልነው የተባለው

ከሁለት አስርት አመታት በላይ የዘለቀው የጸብ ግድግዳ ፈርሶ ሰላምና አንድነት በአካባቢው መታየት ከጀመረ ከረመረም ብሏል።በኢትዮጵያና በኤርትራ በኩል።

ይህን ተከትሎም በድንበር ላይ ሰፍሮ የነበረውን ጦሯን በማንሳት ኤርትራ ለሰላሙ ጥረት ያላትን ጠንካራ አቋም አሳይታለች።

ከአንድ ወር በፊት ደግሞ የሁለቱ ሃገራት ዜጎች ለሰላሙ ያላቸውን ድጋፍ የእርስ በርስ ግንኙነታቸውን በማጠናከር በማሳየት ስራ ተጥምደዋል።

ከሰሞኑ የሁመራ አካባቢ ነዋሪዎች ከዚህ በኋላ የሚለየን የጸብ ግድግዳ አይኖርም ሲሉ የኤርትራዋ ኡምነሃጅር አካባቢ ነዋሪዎች  እስቲ ተገናኝተን በጋራ ጉድያችን ላይ እንምከር ሲሉ ግንቡን አፍርሰው መገናኘታቸው ተሰምቷል።

ሁለቱ ወገኖች ልዩነታቸን አስወግደው በጋራ ጉዳያቸው ላይ ለመምከር ደግሞ አስታራቂ ሽማግሌ አላስፈለጋቸውም።–የራሳቸውን ሃሳብ ራሳቸው ተግባራዊ አደረጉት እንጂ።

ዛሬ ላይ ደግሞ ለዘመናት ሲያወዛግብና የጸብ መነሻ ሲሆን የቆየው የዛላ አንበሳ ድንበር በሁለቱ ሃገራት ዜጎች ስምምነት መከፈቱ ተሰምቷል።

ዛላ አንበሳን አቋርጦ በኤርትራዋ ሰናፌ ወደ ምትገኘው ሰርሃ ከተማ የተጓዘው ቡድን አርባ አባላትን ማካተቱ ተሰምቷል።

የሃይማኖት አባቶች፣የሃገር ሽማግሌዎች፣እናቶችና ወጣቶች ደግሞ በቡድኑ ውስጥ ተካተዋል።

የኤርትራ ወታደሮችም ለቡድኑ አቀባበል እንዳደረጉለት ነው የተሰማው።

በንግድ ከተማነቷ በምትታወቀውና በኤርታራ ደቡባዊ ክፍል የምትገኘው ሰናፌ ለሁለቱ ሃገራት ዜጎች ዲፕሎማሲያዊ ግንኙነት የበኩሏን አስተዋጽኦ እያበረከተች ነው ይላል አዲስ ስታንዳርድ በዘገባው።

እንደ አውሮፓውያኑ ከ1998 ጀምሮ እስከ 2 ሺ ድረስ በሁለቱ ሃገራት መካከል የተካሄደውን የድንበር ውጊያ ተከትሎ አካባቢው ጦርነትም ሰላምም የሌለበት ቀጠና ሆኖ ቆይቷል።

ከዚህም ሌላ ሁለቱም ወገኖች በአካባቢው ከባድ ጦር በማስፈርና ድንበሩን በማካለል ከሁለት አስርት አመታት በላይ አካባቢው በስጋት ሲታመስ ቆይቷል ይላል ዘገባው።

ዛሬ ላይ ግን ያ ታሪክ ተቀይሮ የሁለቱ ሃገር ዜጎች የሚያግዳቸው ድንበር የሚከለክላቸው ሃይል ሳይኖር በጋራ ጉዳያቸው ላይ ለመምከር ሰርሃ ከተማ ገብተዋል።