የወልቃይት ተወላጆች ከፍተኛ ድብደባ ተፈጸመባቸው

(ኢሳት ዲሲ–ጥር 23/2010)

በወልቃይ የወርቅ ቁፋሮ ላይ የተሰማሩ የወልቃይት ተወላጆች ከፍተኛ ድብደባ እንደተፈጸመባቸው ተገልጸ።

ልዩ ስሙ ኢድሪስ በሚባል የወርቅ ክምችት በሚገኝበት ስፍራ በወርቅ ቁፋሮ ስራ በተሰማሩ የወልቃይት ተወላጆች ላይ ድብደባውን የፈጸሙት በትግራይ ፖሊሶች የታገዙ በአካባቢው በሰፈሩ ሰዎች መሆናቸውን የደረሰን መረጃ ያመለክታል።

በሌላ በኩል በወልቃይት የማይጸብሪ ከተማ ነዋሪዎች የተቃውሞ ሰልፍ ማድረጋቸው ተሰምቷል።

ተቃውሞው በማንነታችን በእኩል እየታየን አይደለም በሚል እንደሆነ መረጃዎች ያመለክታሉ።

የትግራይ ህዝብ ነጻ አውጪ ግንባር ህወሃት አዲስ አበባን ከመቆጣጠሩ በፊት ጀምሮ የትግራይ ተወላጆች እንዲሰፍሩ ከተደረጉባቸው አካባቢዎች አንዱ ኢድሪስ ይባላል።

ይህ አካባቢ በወርቅ ምርት የበለጸገ እንደሆነ ይነገርለታል።

የትግራይ ህዝብ ነጻ አውጪ ግንባር ህወሃት በ1983 ኢትዮጵያን ከተቆጣጠረ በኋላ በብዛት የትግራይ ተወላጆች በኢድሪስ በመስፈር ወርቅ እያመረቱ መጠቀም ጀምረዋል።

ነባሮቹ የአካባቢው ነዋሪዎች የሆኑት የወልቃይት ተወላጆች መገፋት የጀመሩትም እነዚህ የትግራይ ሰፋሪዎች አካባቢውን ከተቆጣጠሩት በኋላ ነው።

ኢሳት ያነጋገራቸውና ለጊዜው ድምጻቸው እንዳይሰማ የጠየቁት የወልቃይት ተወላጆች እንደሚሉት በትግራይ ሚሊሻና በትግራይ ፖሊስ ድጋፍ የሚደረግላቸው ሰፋሪዎች ነባሩን እያስለቀቁ የወርቅ ምርቱን ተቆጣጥረውታል።

በወርቅ ቁፋሮ የተሰማሩ በመቶዎች የሚቆጠሩ የወልቃይት ተወላጆች ባልፉት ዓመታት ደብዛቸው መጥፋቱን የሚገልጹት ነዋሪዎች እንደ ሁለተኛ ዜጋ የሚታዩበት ሁኔታ መፈጠሩን በቁጭት ያነሳሉ።

ሰሞኑን ኢድሪስ በተባለው የወርቅ ማውጫ ስፍራ የተፈጸመውም ተመሳሳይ ተግባር ነው።

በአካባቢው ሁሌም ራሳቸው ብቻ ተጠቃሚ እንዲሆኑ የሚፈልጉት ከትግራይ የመጡ ሰፋሪዎች በወልቃይት ተወላጆች ላይ ከፍተኛ ድብደባ መፈጸማቸውን የደረሰን መረጃ አመልክቷል።

የሰሜን ወሎ ህዝባዊ ንቅናቄን ተከትሎ በወልቃይት አመጽ ሊነሳ፣ጥቃት ሊደርስብን ይችላል በሚል የሰጉ የትግራይ ሰፋሪዎች በትግራይ ፖሊስ ታግዘው በወርቅ ቁፋሮው አካባቢ በሚኖሩ የወልቃይ ተወላጆች ላይ ድብደባውን መፈጸማቸውን ነው ነዋሪዎቹም ለኢሳት የገልጹት።

‘’እናንተ ወልቃይቶች አማራ ነን ብላችኋል። ይህ መሬት የትግራይ ነው። ስለዚህ ወርቅ መቆፈር አትችሉም’’ መባላቸውን የሚጠቅሱት የወልቃይት ተወላጆች ከ20 በላይ በሚሆኑት ላይ የትግራይ ሰፋሪዎች ከፍተኛ ድብደባ ፈጽመዋል። ጉዳትም አድርሰዋል ሲሉ ገልጸዋል።

ይህን ሲያደርጉ የትግራይ ፖሊሶች በአቅራቢው ነበሩ።

የወልቃይት ተወላጆችን የያዙትን የቁፋሮ መሳሪያዎች እንዲያስቀምጡ በማስገደድ በሰፋሪዎቹ እንዲደበደቡ ማድረጋቸውን ለማወቅ ተችሏል።

የአጸፋ ርምጃ በሚወስዱ የወልቃይት ተወላጆች ላይ ፖሊሶቹ ተደርበው ጥቃት ይፈጽሙ እንደነበርም የደረሰን መረጃ አመልክቷል።

ከፍተኛ ጉዳት የደረሰባቸው ወደ ሆስፒታል መወሰዳቸውም ታውቋል። በዚህን ወቅት የደረሰ የሞት አደጋ ስለመኖሩ የታወቀ ነገር የለም።

በሌላ በኩል በወልቃይት ማይጸብሪ በምትባል ከተማ ነዋሪዎች የተቃውሞ ሰልፍ ማድረጋቸውን ለኢሳት በደረሰው መረጃ ላይ ተመልክቷል።

ትላንት በተካሄደው በዚሁ ሰልፍ የወልቃይት ተወላጆች በእኩል እየታየን አይደለንም ሲሉ ድምጻቸውን አሰምተዋል።

የትግራይ ክልል አካል ናችሁ ከተባልን ለምን እንደትግራይ ህዝብ በእኩልነት አንኖርም የሚል ጥያቄ አንስተው አደባባይ የወጡት የወልቃይት ተወላጆች ከፖሊስ ጋር መጋጨታቸው ታውቋል።

የተገደሉ ሰዎች እንዳሉ ቢነገርም ኢሳት ማረጋገጥ አልቻለም።