የእነ ጋዜጠኛ እስክንድር ነጋ መልሶ መታሰር ተወገዘ

(ኢሳት ዲሲ–መጋቢት 18/2010) አለማአቀፉ የፕሬስ ተቋም የእነ ጋዜጠኛ እስክንድር ነጋን መልሶ መታሰር በጽኑ አወገዘ።

ተቋሙ እስክንድር ነጋን ጨምሮ እንደገና የታሰሩ ጋዜጠኞችና ፖሊቲከኞች በአስቸኳይ እንዲለቀቁ ጥሪ አድርጓል።

የእነ እስክንድር ነጋ መልሶ መታሰር በኢትዮጵያ የስርአት ለውጥ እንደሚያስፈልግ አመላካች መሆኑን ደግሞ አምንስቲ ኢንተርናሽናል ገልጿል።

የአለም አቀፉ የፕሬስ ተቋም/አይፒአይ/ምክትል ዳይሬክተር ስኮት ግሪፊን እንዳሉት ከዚህ ቀደም እስረኞች ሲለቀቁ በኢትዮጵያ መልካም ነገር ይመጣል የሚል ተስፋ ተሰንቆ ነበር።

ይህም ሆኖ ግን የእነ እስክንድር ነጋ ተመልሶ መታሰር እጅግ የሚያበሳጭና ተስፋን የሚያጨልም መሆኑን ምክትል ዳይሬክተሩ ገልጸዋል።

እናም አስቸኳይ ጊዜ አዋጁ ሕግና ስርአትን ለማስከበር የወጣ ሳይሆን ዜጎችን አፍኖ ለመግዛት ያለመ መሆኑን ያሳያል ነው ያሉት።

የአለምአቀፍ የፕሬስ ተቋም ምክትል ዳይሬክተር ስኮት ግሪፊን እንዳሉት እስክንድር ነጋን ጨምሮ በቁጥጥር ስር የዋሉት ጋዜጠኞችና ፖለቲከኞች በአስቸኳይ ሊለቀቁ ይገባል።

ይሕ በእንዲህ እንዳለም የእነ እስክንድር ነጋ፣አንዱዓለም አራጌ እና ሌሎች ጋዜጠኞችና ፖለቲከኞች ተመልሶ መታሰር በኢትዮጵያ የስርአት ለውጥ እንደሚያስፈልግ አመላካች መሆኑን አምንስቲ ኢንተርኛሽናል ገልጿል።

የድርጅቱ የምስራቅ አፍሪካ የሰብአዊ መብት ተከራካሪ አቶ ፍስሐ ተክሌ ለአሜሪካ ድምጽ እንደገለጹት ደግሞ እስሩ በኢትዮጵያ ሕግና ስርአት እንደሌለ ያመለክታል።

ሰዎችን እየፈቱ ማሰር ለውጥ እንደማያመጣም ነው የገለጹት።

ከዚህ ቀደም የፖለቲካ እስረኞች መለቀቃቸው መልካም የነበረ ቢሆንም እንደገና መታሰራቸው ግን ሕገ ወጥ ነው ብለዋል።

መንግስት የፖለቲካና የዲሞክራሲ ምህዳሩን አሰፋለሁ በሚል የገባው ቃልም ከንቱ መሆኑን እንደሚያሳይም አቶ ፍስሀ ገልጸዋል።