የአማራ ክልል ወጣቶች ማህበር ፕሬዚዳንት ከአገር ተሰደደ

ሐምሌ ፳፮ (ሀያ ስድስት) ቀን ፳፻፬ ዓ/ም

ኢሳት ዜና:-የአማራ ክልል የወጣቶች ማህበር ፕሬዚዳንት በመሆን ያገለገለው፣ በክልሉ ውስጥ በወጣቱ ዘንድ ከፍተኛ ከበሬታ ያተረፈውና ወጣቱን ለለውጥ ለማንቀሳቀስ ከፍተኛ ስራ መስራቱ የሚነገርለት ወጣት ዘመነ ካሴ እንዲሁም የህግ ምሩቃን የመሰረቱት የአባይ ፍሬዎች ወጣቶች ማህበር ሊቀመንበር የሆነው ከፍያለው ጌጡ ከገዢው ፓርቲ የደህንነት ሰዎች ክትትል አምልጠው ወደ ሶስተኛ አገር ተሰደዋል።

ወጣት ዘመነና ወጣት ከፍያለው  በስደት ካሉበት ቦታ ከኢሳት ጋር ሰፊ ቃለምልልስ አድርገዋል።

የአማራ ክልል ወጣቶች የመንግስት ባለስልጣናትን “እስከዛሬ በስማችን ስትቀልዱ ኖራችሁዋል፣ ከእንግዲህ ወዲያ ግን ይበቃችሁዋል” እያለ መሆኑን ዘመነ ተናግሯል

ከአማራ ክልል ከፍተኛ ባለስጣናት ጋር በመሆን ለረጅም ጊዜ መስራቱን የሚገልጠው ዘመነ ፣ ብአዴን ማለት አማርኛ ተናጋሪ የህወሀት ክንፍ ነው ይላል

የኢህአዴግ ካድሬዎች የክልሉን ሰራተኛ በአውራጃ በመከፋፋል ፣ ህዝቡ በአንድነት እንዳይነሳ ከፍተኛ ስራ እንደሚሰሩ፣ ወጣት ዘመነ በቅርብ የተመለከተውን መስክሯል

የአማራው ክልል በህወሀት ሰዎች የሚተዳዳር መሆኑን የሚናገረው ወጣት ዘመነ ካሴ፣ የህወሀት ባለሀብቶች የክልሉ ባለስልጣናትን በጥቅም እንደያዙአቸው ይናገራል።

የአቶ መለስ ዜናዊ ከስልጣን መራቅ ብአዴን አንሰራርቶ የስልጣን ተቃናቃኝ ሆኖ እንዲወጣ ያደርገዋል ብለህ ታስባለህ ተብሎ ለተጠየቀው  ወጣት ዘመነ ሲመልስ፣ ህወሀት ስልጣንኑን በሞኖፖል መቆጣጠሩ የብአዴን አባላትን ሁሌም የሚቃወሙት መሆኑን በማስታወስ፣ ይሁን እንጅ በአውራጃ መከፋፈላቸውን እስካላቆሙና በአንድነት እስካልተነሱ ድረስ ህወሀት ገናና ሆኖ ሊቀጥል እንደሚችል ተናግሯል።

የአረቡ አብዮት ከተጀመረ በሁዋላ፣ የክልሉ ወጣቶች በህቡእ እየተደራጁ መሆኑን ወጣት ዘመነ ገልጧል

 

የአባይ ፍሬዎች ወጣቶች ማህበር ሊቀመንበር የሆነው ወጣት ከፍያለው ጌጡ በበኩሉ ማህበራቸው ኢህአዴግን አልደገፈም በሚል ከፍተኛ ችግር ደርሶባቸው እንደነበር ተናግሯል ።

ውድ ተመልካቾቻችን ከሁለቱ የወጣት መሪዎች ጋር ያደረግነውን ቃለምልልስ ሙሉውን ክፍል በቅርቡ እንደምናቀርብ ለመግለጥ እንወዳለን።

___________________________________________________________________________________________________________________________________________________

ESAT is the first independent Ethiopian satellite service tasked to produce accurate and balanced news and information, as well as other entertainment, sports and cultural programming created for and by Ethiopians.

ESAT is committed to the highest standards of broadcast journalism and programming and will strive to provide an outlet of expression to all segments of the diverse Ethiopian community worldwide