የትግራይ ህዝብ መካስ አለበት ተባለ

(ኢሳት ዲሲ–ጥር 9/2010)

የትግራይ ህዝብ ከማንም በላይ ውድ ዋጋ የከፈለ በመሆኑ መካስ አለበት ሲሉ የህወሃት የስራ አስፈጻሚ ኮሚቴ አባልና ቃል አቀባይ ገለጹ።

ቃል አቀባዩ አቶ ጌታቸው ረዳ የህወሀትን 7ኛ ድርጅታዊ ጉባዔ አስመልክቶ በሰጡት ጋዜጣዊ መግለጫ ላይ እንደገለጹት የትግራይን ህዝብ ለመካስ አዲሱ አመራር ቆርጦ ተነስቷል።

በኢትዮጵያ በክልሎች መካከል ሰፊ የልማትና የእድገት ልዩነት ፖለቲካዊ ቀውስ በፈጠረበት በዚህን ወቅት የአቶ ጌታቸው ረዳ መግለጫ ቀውሱን ይበልጥ ሊያባብሰው እንደሚችል ታዛቢዎች ይገልጻሉ።

የ2016 የኢትዮጵያ መንገዶች ባለስልጣን መረጃ እንደሚያመለክተው ከህዝብ ብዛትና ከቆዳ ስፋት አንጻር በትግራይ ክልል የተሰራው የአስፋልት መንገድ ከሌሎች ክልሎች በብዙ እጥፍ የሚበልጥ ነው።

በሆስፒታል ተጠቃሚነት የትግራይ ክልል በቀዳሚ ስፍራ ላይ ይገኛል። በትግራይ አንድ ሆስፒታል ለ285ሺህ ሰው አገልግሎት ሲሰጥ በአማራ ክልል አንድ ሆስፒታል ከ1ሚሊየን በላይ ለሆነ ህዝብ የሚዳረስ ነው።

በኦሮሚያ 1 ሆስፒታል ለ900ሺህ ሰው አገልግሎት ይሰጣል።

6 ሚሊየን ህዝብ ባላት በትግራይ በሶስት ከተሞች ዘመናዊ የአውሮፕላን ማረፊያዎች ሲገነቡ ከ5 እጥፍ በላይ የህዝብ ብዛት ባለው የኦሮሚያ ክልል በሁለት ከተሞች ብቻ እንዳለ መረጃዎች ያመለክታሉ።

ከ66 በላይ ኩባንያዎች ያሉት የትግራይ መልሶ ማቋቋሚያ ድርጅት ኤፈርት በትግራይ ክልል ከ100ሺህ በላይ የስራ እድል ፈጥሯል። ንጽጽሩ ብዙ ነው። በየዘርፉ የሚታየው ልዩነት ግልጽ ነው።

በዩኒቨርስቲ ብዛትና ጥራት፣ በኤሌክትሪክ አቅርቦትና በኢንዱስትሪ ግንባታ በትግራይና በሌሎቹ የኢትዮጵያ ክልሎች መካከል ያለው ልዩነት ላለፉት ሁለት አስርት ዓመታት የኢትዮጵያ የፖለቲካ ቀውስ ዋነኛ ማጠንጠኛ ሆኖ ዘልቋል።

የእድገትና የልማት ልዩነቱን ዓለም ዓቀፍ ተቋማት ጭምር በመረጃ አስደግፈው በማሳየት ላይ ሲሆኑ ወደ አንድ አካባቢ ያደላው ተጠቃሚነት ኢትዮጵያን ወደ እርስ በእርስ ጦርነት እንዳይከታት ስጋቱ ከየአቅጣጫው እየተሰማ ነው።

መቀሌ ላይ እየተካሄደ ባለው የህዝባዊ ወያኔ ሀርነት ትግራይ ህወሀት 7ኛ ድርጅታዊ ጉባዔ አስመልክቶ ለጋዜጠኞች መግለጫ የሰጡት የህወሀቱ ቃል አቀባይ አቶ ጌታቸው ረዳ የትግራይ ህዝብ ከከፈለው መስዋዕትነት አንጻር ያገኘው በጣም ኢምንት ነው።

የትግራይ ህዝብ አሁንም በከፈለው ዋጋ መጠን ውለታ ይቅርና ከሩብ በላይ ህዝብ አሁንም በመራራው ድህነት ስር የሚኖር ህዝብ ነው ያሉት አቶ ጌታቸው ከማንም በላይ ውድ ዋጋ የከፈለው ይህ ህዝብ የሚካስበት ጊዜ አሁን ነው ብለዋል።

ሳይበላ በልቷል እየተባለ የውሸት ሪፖርት የሚቀርብ መሆኑን የጠቀሱት አቶ ጌታቸው አዲሱ አመራር የትግራይን ህዝብ ለመካስ ተዘጋጅቷል ማለታቸውን ከምንጮች መረጃ ለማወቅ ተችሏል።

አምባገነኑ የደርግ ስርዓት ያንበረከከው የትግራይ ህዝብ በዚህ ዘመን የቀበሌ አመራሮችን እንዲፈራ ተደርጓልም ሲሉ ተናግረዋል።

የትግራይ ህዝብ አስቸጋሪ ሁኔታ ውስጥ ነው ያለው አዲሱ አመራር ይሄን ህዝብ ከዚህ ችግር ለማላቀቅ ቆርጦ ተነስቷል ብለዋል ቃል አቀባዩ።

ኢሳት ያነጋገራቸው የፖለቲካ ምሁራን በኢትዮጵያ የተዛባ የእድገት ልዩነት እንዲፈጠር በማድረግ ሀገሪቱን ለከፍተኛ አደጋ የዳረገው ህወሃት የትግራይን ህዝብ ይበልጥ ተጠቃሚ አድርጎ መነሳቱ የተቀጣጠለውን ህዝባዊ አመጽ ያባብሰዋል ብለዋል።