የተንዳሆ ስኳር ፋብሪካ ማምረት ካቆመ አራት ወራት ማስቆጠሩ ተገለጸ

(ኢሳት ዲሲ–መጋቢት 23/2011)የተንዳሆ ስኳር ፋብሪካ ማምረት ካቆመ አራት ወራት ማስቆጠሩን በፋብሪካው ተቀጥረው የሚሰሩ የአካባቢው ነዋሪዎች ገለጹ።

ነዋሪዎቹ ለኢሳት እንዳሉት ፋብሪካው ለምን ተዘጋ ለሚለው ጥያቄያችን ምላሽ ማግኘት ባለመቻላችንም ወደ ፋብሪካው የሚወስደውን መንገድ ዘግተናል።

መንገዱ ከተዘጋም አራት ቀናትን አስቆጥሯል ብለዋል።

ዋነኛ ጥያቄያችንም ይላሉ ፋብሪካውን እየመሩ ያሉት ሰዎች ትላንት ፋብሪካውን ሲመዘብሩ የነበሩ ስለሆኑ ከቦታቸው ይነሱ፣ ፋብሪካውም በሙሉ አቅሙ ወደ ስራ ገብቶ እኛም ሃገራችንም ተጠቃሚ እንሁን የሚል ነው ብለዋል።

እነሱ እንደሚሉት 10 አመታትን በቦታው ላይ ተተክሎ ቢቆይም የሰራው ስራና የተገኘው ነገር ግን የማይገናኝ ነው ።–በአመት ፋብሪካውን የሚያመርተው ለሶስት ወር ብቻ መሆኑን በመጠቆም።

ሰራተኞቹ ፋብሪካው የሚያስገባው ገቢና የማይመጣጠነውን ወጪውንም የማይገባና ምዝበራ የተሞላበት ሲሉ ያነሳሉ።

የኛ ጥያቄ የወጣት ተጧሪዎች አንሁን።እንስራና ፋብሪካውን እንጥቀም እኛም እንጠቀም ለዚህ ደግሞ የሚመለከተው አካል መልስ ይስጠን ብለዋል።

በተደጋጋሚ ያነሳነው ጥያቄ ምላሽ ማግኘት ባለመቻሉም ወደ ፋብሪካው የሚወስደውን መንገድ ዘግተን ጥያቄያችን እንዲመለስ እየጠበቅን ነው ብለዋል ከኢሳት ጋር ባደረሱት መረጃ።