የተመድ የሰብዓዊ መብት ከፍተኛ ኮሚሽነር ከእስር ከተፈቱት ታዋቂ ሰዎችና ከፖለቲካ ድርጅት መሪዎች ጋር ተነጋገሩ

የተመድ የሰብዓዊ መብት ከፍተኛ ኮሚሽነር ከእስር ከተፈቱት ታዋቂ ሰዎችና ከፖለቲካ ድርጅት መሪዎች ጋር ተነጋገሩ
(ኢሳት ዜና ሚያዝያ 17 ቀን 2010 ዓ/ም) የተመድ የሰብዓዊ መብት ከፍተኛ ኮሚሽነር ዘይድ ራአድ አል ሁሴን ከተቃዋሚ ፖለቲከኞች፣ የሃይማኖት አባቶች፣ የሰብዓዊ መብት ተሟጓቾችና ጋዜጠኞች ጋር ተወያይተዋል።
ኢትዮጵያን በመጎብኘት ላይ ያሉት ኮሚሽነሩ በኢትዮጵያ የሰብዓዊ መብት ዙሪያ እና አገሪቱ መውሰድ ስለሚገባት እርምጃ አስተያቶችን ሰብስበዋል።
በገዥው ፓርቲ ባለስልጣናት ወደ ኢትዮጵያ እንዳይገቡ ከተከለከሉ ከሁለት ዓመት በኋላ ድጋሚ ተፈቅዶላቸው እንዲመጡ መደረጉን የሚገልጹት ባለስልጣኑ፣ የተመድ የሰብዓዊ መብት ኮሚሽን ቢሮ አዲስ አበባ ላይ ለመክፈት መዘጋጀታቸውን ገልጸዋል። በተወያዮቹ በአገሪቱ መጠነ ሰፊ የሆነ የሰብዓዊ መብት ጥሰቶች እንደሚፈጸሙ ለኮሚ ነሩ ገልጸውላቸዋል። አሁን ያለው አመራር ጥገናዊ ለውጥ ለማምጣት የሚሰራ ከሆነ አገሪቱ ወደነበረችበት ችግር ዳግም ትገባለች ሲሉ ተወያዮቹ አጽኖት አስጠንቅቀዋል።
በውይይቱ ላይ የተሳተፈው በቅርቡ ከእስር የተፈታው ዮናታን ተስፋዬ እንዳለው ”እውነተኛ የሆነ አገራዊ ለውጥ ሊመጣ የሚችለው አገዛዙ የሚከተለውን ኢዲሞክራሲያዊ አስተሳሰብ መቀየር ሲችል ነው። ‘ከኔ ውጪ ያለው ጠላት ነው’የሚለው ኢዲሞክራሲያዊ አስተሳሰብን የመሰረተው የአብዮታዊ ዴምክራሲያዊ ርእዮተ ዓለም ተቀይሮ አዲስ የስርዓት ለውጥ ሲመጣ ብቻ ነው።”
ከዋልድባ ገዳም ተይዘው ካለ ፍትሕ ታስረው ሰቆቃ የተፈጸመባቸው የሃይማኖት አባቶች አባ ገብረኢየሱስ ኪዳነማርያም እና አባ ገብረስላሴ ወልደሃይማኖት፣ ጋዜጠኛ እስክንድር ነጋ፣ አንዱአለም አራጌ፣ ዮናታን ተስፋዬ፣ ንግስት ይርጋ፣ የዞን 9 ጦማሪያንን ጨምሮ ጦማሪና መምህር ስዩም ተሾመ፣ ወ/ት ወይንሸት ሞላና ሌሎችም በአካል ተገኝተው በስር ቤቶች በምርመራ የተፈጸመባቸውን የሰብአዊ መብት ጥሰት በዝርዝር አስረድተዋል። በተጨማሪም በተለያዩ እስር ቤቶች ውስጥ ያሉ የፖለቲካ እስረኞችን ጨምሮ፣ በቂሊንጦ እስር ቤት ቃጠሎ በሃሰት ተከሰው ያሉ 38 እስረኞች ካለምንም ቅድመ ሁኔታዎች እንዲፈቱ ጠይቀዋል።
ኮሚሽነር ዘይድ በኢትዮጵያ ጉዳይ ቀጣይ ተስፋ እንዳላቸው የተናገሩ ቢሆንም፣ ተሰብሳቢዎቹ ግን ገዥው ፓርቲ ከቃል በዘለለ ተግባራዊ ሥራዎችን ማሳየት አለበት ብለዋል። ኮሚሽነሩ ጠቅላይ ሚንስትሩን ጨምሮ ከሚመለከታቸው ባለስልጣናት ጋር ውይይት ያደርጋሉም ተብሎ ይጠበቃል።
አሜሪካ የውጭ ጉዳይ መስሪያ ቤት ሰሞኑን ባወጣው ሪፖርት በምዕራባውያን አቆጣጠር በ2016 ወይም በ2009 ዓም ብቻ የሶማሊ ክልልን ጨምሮ በትንሹ 769 ሰዎች መገደላቸውን ጠቅሷል።