የብአዴን አጠቃላይ ስብሰባ በገጠመው የከፋ ተቃውሞ ወደ ዋናው የስብሰባ አጀንዳ መግባት እንደተሳነው ታወቀ

(ኢሳት ዜና–መስከረም 17/2010) የብአዴን አጠቃላይ ስብሰባ በ4ኛ ቀን ውሎው በገጠመው የከፋ ተቃውሞ ወደ ዋናው የስብሰባ አጀንዳ መግባት እንደተሳነው ታወቀ።

የራያ ጉዳይ ተጨምሮበት ስብሰባው በጭቅጭቅና ሃይለቃል በተሞላበት ምልልስ በቀጠሉን የኢሳት ምንጮች ገልጸዋል።

የግጨው፣የወልቃይትና የራያ ጉዳይ እያለ ሌላ አጀንዳ አያስፈልገንም ያሉት ተሳታፊዎች የብአዴንን መሪዎች በጥያቄ ወጥረው መያዛቸው ተሰምቷል።

በተለይ በአቶ ገዱ አንዳርጋቸው ላይ የሚወረወሩት ተራ የሚባሉ አይነት ስድቦች ስብሰባውን የከፋ እንዲሆን ማድረጉን ነው ምንጮቹ የገለጹት።
የትግራይ የበላይነት ጉዳይም ሌላው የውዝግብ ርእስ መሆኑ ታውቋል።

ባለፈው ዕሁድ የተጀመረውና ለ10 ቀናት የሚዘልቀው የብሄረ አማራ ዴሞክራሲያዊ ንቅናቄ ብአዴን አጠቃላይ ጉባዔ ወደ አጀንዳ መግባት ሳይችል 4ኛ ቀኑን ተሻግሯል።

ይህ ጉባዔ የብአዴን ማዕከላዊ ኮሚቴ የባለፈው ሳምንት ስብሰባ ያለስምምነት መበተኑን ተከትሎ የተጠራ ቢሆንም በተቀረጹት የጉባዔው ሁለት አጀንዳዎች ላይ ለመነጋገር ከተሳታፊዎች ተቃውሞ በመቅረቡ ለአምስተኛ ቀን መተላለፉን የኢሳት ምንጮች ገልጸዋል።

በብአዴን የተቀረጹትና ለውይይት የተዘጋጁት ሁለቱ አጀንዳዎች እየሰራን እንታደሳለን የሚለውና የንቅናቄውን የ2010 የስራ ዕቅድ የተመለከተ ነበር።

ሆኖም ተሳታፊዎች የግጨው፣ የወሎ ራያና የወልቃይት ጉዳይ እያለ ሌላ አጀንዳ አያስፈልግም በማለቱ እስከዛሬ ዋናዎቹ አጀንዳዎች ሳይነኩ ቀርተዋል።
የትግራይ የበላይነት በዚህ ስብሰባም አንገብጋቢ ርዕስ ሆኖ በተሳታፊው ተነስቷል።

ባለፈው ሳምንት ያለስምምነት የተበተነውና ብአዴንን ያንገጫገጨው ስብሰባ ንቅናቄው በሶስት ሃይሎች ተወጥሮ ወደፊት እንዳይራመድ እንዳደረገው ይነገራል።

ለህዝባዊ ወያኔ ሀርነት ትግራይ ህወሀት ጥብቅና በመቆም የሚታወቁና ከአማራው ይልቅ ለህወሀት ጥቅም ቅድሚያ በመስጠት የሚወነጀሉት በአቶ አለምነው መኮንን የሚመሩት የብአዴን አመራሮች የበላይነትን በያዙበት ስብሰባ በተለይ አቶ ገዱ አንዳርጋቸውና ዶ/ር አምባቸው መኮንን ላይ ያነጣጠረ ጥቃት መሰንዘሩን የኢሳት ምንጮች ገልጸዋል።

ምንም እንኳን 65ቱ የማዕከላዊ ኮሚቴ አባላት የማናውቀው ስምምነት ብለው የግጨው ጉዳይ ላይ ጥያቄ ቢያነሱም አቶ ዓለምነው መኮንን በሰከነ ሁኔታ የተቋጨ ነው የሚል ሪፖርት ማቅረባቸው ተገልጿል።

“ለረዥም ጊዜ በሁለቱ ክልሎች እና ድርጅቶች መካከል መከፋፈልና ለጎሪጥ መተያየትን እንዲሁም ለጠላት በተለይም ለትምክህተኛው ኃይል መጠቀሚያ ሆኖ የቆየው የትግራይ እና የአማራ የወሰን የይገባኛል ውዝግብና የግጨው ጉዳይ እጅግ በሰከነ እና ህዝብን ባማከለ መንገድ መፍትሔ አግኝቷል።

ይህን የስራ አስፈፃሚ ውሳኔ ማዕከላዊ ኮሚቴው ተቀብሎ ለድርጅቱ አባላትና ለህዝቡ እዲያሳምን ስራ አስፈፃሚው ወስኗል ” የሚለው የአቶ ዓለምነው ሪፖርት በማዕከላዊ ኮሚቴ አባላቱ ከፍተኛ ተቃውሞ የገጠመው ሲሆን ስብሰባው ያለስምምነት እንዲበተን እንዳደረገው የሚታወስ ነው።

የማዕከላዊ ኮሚቴ አባላቱ አቶ ገዱ ላይ አቋም ይዘው ባፋጠጡበት መድረክ የአቶ በረከት ስምዖን አስተያየት ለጊዜው አቶ ገዱን ትንፋሽ እንዲወስዱና ተነጥለው እንዳይመቱ እንዳደረጋቸው ከውስጥ ምንጮች የተገኘው መረጃ አመልክቷል።

በወቅቱ አቶ በረከት ስምዖን ከአቶ ገዱ ጋር የተሰለፉበት ምክንያት ብአዴን ውስጥ የተፈጠረው መከፋፈል አሳስቧቸው ሊሆን እንደሚችልም ይነገራል።

ያለስምምነት የተበተነው የማዕከላዊ አባላቱ ስብሰባ ለአጠቃላዩ ጉባዔ መጠራት ምክንያት እንደሆነ ተገልጿል።

ዕሁድ የተጀመረው አጠቃላዩ ስብሰባ ግጨውን ጨምሮ በሃይል ወደትግራይ ክልል የተጠቃለሉ አካባቢዎችን በማንሳት ሃይለቃልና ስድቦች የተሞሉበት ሙግት እንደነበር ምንጮች ገልጸዋል።

እነዚህ ጉዳዮች ላይ ስምምነት ሳይደረስ ወደ ተዘጋጁት አጀንዳዎች አንገባም የሚለው የተሳታፊው አቋም አሸናፊ ሆኖ ወጥቷል ተብሏል።

ዛሬ እስከምሳ ሰዓት ድረስ የተዘጋጁት አጀንዳዎች ያልተነኩ ሲሆን ከመድረክ የብአዴን መሪዎች ለማግባባት ያደረጉት ጥረት ከተሳታፊዎች በገጠማቸው በስድብ የታጀበ ተቃውሞ ምክንያት በአቋማቸው መግፋት ሳይችሉ ቀርተዋል።

የሞባይል ስልክን ጨምሮ ማንኛውም የመገናኛ መሳሪያ እንዳይገባ በጥብቅ ተከልክሎ እየተካሄደ ባለው የብአዴን አጠቃላይ ጉባዔ የትግራይ የበላይነት ትልቁ መወያያ ርዕስ ሆና መውጣቱ ታውቋል።

ተሳታፊዎቹ ለብአዴን መሪዎች ተላላኪና የህወሀት ጉዳይ አስፈጻሚ እንደሆኑ በመግለጽ የአማራ ህዝብ አፍሮባችኋል ማለታቸውን ያገኘነው መረጃ ያመለክታል።