የቀድሞ የኤሳዋን ሃላፊዎች በድርጊታቸው ተጸጽተው በሰሜን አሜሪካ የኢትዮጵያ ስፖርት ፌዴሬሽንና (ESFNA) የኢትዮጵያን ህዝብ ይቅርታ ጠየቁ

(ሃምሌ 22 ፥2008)

ከኢትዮጵያ የስፖርት ፌዴሬሽን በሰሜን አሜሪካ (ESFNA) ተለይተው የራሳቸውን ድርጅት ካቋቋሙት የቀድሞውን ፕሬዚደንት ጨምሮ ሁለቱ በድርጊታቸው ተጸጽተው ፌዴሬሽኑን እንዲሁም የኢትዮጵያን ህዝብ ይቅርታ ጠየቁ።

ኤሳዋን የተባለውና በእነርሱ ጎራ ያቋቋሙት ድርጅት ውስጥ የተፈጠረውን የገንዘብ ብክነት በተመለከተ ለኢሳት የደረሰው መረጃ ትክክል እንደነበርም አረጋግጠዋል።ESFNA

የኢትዮጵያ ሳተላይት ሬዲዮና ቴለቪዥን አገልግሎት ስለ “ኤሳዋን” የደረሰውን የውስጥ መረጃ ለህዝብ ይፋ ማድረጉን ተከትሎ ተጨማሪ ማስረጃዎች አሉን በማለት በኢሳት ስቱዲዮ በአካል የተገኙት አቶ እያያ አረጋ እና አቶ ታምሩ አበበ፣ እንዲሁም በስልክና ጎግል ሃንግአውት (google Hangout) የቀረቡት አቶ ሳሙዔል ሃይሌ እና አቶ ጸጋዬ ልዑል ሲሆኑ፣ መረጃዎቹን በዝርዝር አቅርበዋል።

ከዛሬ 33 አመት በፊት በሰሜን አሜሪካ የኢትዮጵያ ስፖርት ፌዴሬሽን (ESFNA) ምስረታ ውስጥ በግንባር ቀደምትነት የተሳተፉ እንዲሁም በፌዴሬሽን አመራር ውስጥ እስከ ምክትል ፕሬዚደንትነት አገልግለው የነበሩት አቶ እያያ አረጋ ከዋናው ፌዴሬሽን ተለይተው ከወጡ በኋላ ኤሳዋን ተብሎ በሚጠራው ድርጅት ውስጥ በፕሬዚደንትነት ማገልገላቸውን አስታውሰው፣ በድርጅቱ ውስጥ ታይቷል የሚሉትን ህገወጥ እና የቤተሰት አሰራር ይፋ አድርገዋል።

አቶ እያያ አረጋ ለኢሳት የደረሰ የሰነድና የድምፅ ማስረጃ ትክክለኛ መሆኑን አረጋግጠው በቀረበው ድምፅ ውስጥ የእሳቸው ንግግርም እንዳለበት አክለው ገልጸዋል።

አቶ እያያ አረጋ በመግለጫቸው እንዳስታወቁት ከሆነ፣ እኤአ ነሃሴ 7 ቀን 2012 በተደረገው ስብሰባ ነባር አመራሩ ስንብት አድርጎ በወጣት አመራሮች እንዲተካ የተወሰነ ቢሆንም አቶ አብነት ገ/መስቀልና አቶ ብስራት ገ/መስቀል ውሳኔውን በመሻር አመራሩን ህገወጥ በሆነ መልኩ እንደተቆጣጠሩት አስታውቀዋል። ሁለቱ ወድማማቾች የድርጅቱ ስፖንሰር ከሆኑት ሼህ መሃመድ አላሙዲን የተበላሸውን 335 ሺህ ዶላር ወደ ግላቸው አዙረዋል በማለት ገልጸዋል።

ኢትዮጵያን ከብሄራዊ ቡድን ተሰልፎ ከመጫወት ጀምሮ ያገለገለው አቶ እያያ አረጋ እና የኤሳዋን ገንዘብ ያዥ የነበረው አቶ ታምሩ አበበ በማወቅም ሆነ ባለማወቅ ለሰሯቸው ስህተቶች የኢትዮጵያን ህዝብ ይቅርታ ጠይቀዋል።