የሶማሌ ተወላጆችን በቁጥጥር ስር ለማዋል የሶማሌ ክልል ፍቃደኛ አይደለም ተባለ

(ኢሳት ዜና–ሕዳር 20/2010)በኦሮሚያና በሶማሌ ክልል በነበረው ግጭት ተጠርጣሪ የሆኑ የሶማሌ ተወላጆችን በቁጥጥር ስር ለማዋል የሶማሌ ክልል ፍቃደኛ እንዳልሆነ ተገለጸ።

በቁጥጥር ስር ለማዋል ተባባሪ ያልሆኑ የሶማሌ ክልል አመራሮች ርምጃ እንዲወሰድባቸው ተወስኗል።

በኦሮሚያና ሶማሌ ክልሎች ለወራት በዘለቀውና አሁንም መብረድ ባልቻለው ግጭት የተጠረጠሩ ግለሰቦችን አሳልፎ ለመስጠት ፈቃደኛ ያልሆኑ የሶማሌ ክልል አመራሮች ርምጃ እንዲወሰድባቸው መወሰኑን የዘገበው በሀገር ውስጥ የሚታተመው ሪፖርተር ጋዜጣ ነው።

ውሳኔውን ያሳለፈው በምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ደመቀ መኮንን የሚመራው ግብረ ሃይል እንደሆነም ዘገባው አመልክቷል።

ግብረ ሃይሉ የፌደራል ፖሊስ ያቀረበውን ሪፖርት ካዳመጠ በኋላ የተጠረጠሩትን በሕግ ጥላ ስር ለማዋል በተደረገ ጥረት ተባባሪ ያልነበሩ የክልሉ አመራሮች ተጠያቂ እንዲሆኑ መመሪያ አስተላልፏል።

የፌደራል ፖሊስ በዚህ ሪፖርቱ ተጠርጣሪዎችን በቁጥጥር ስር ለማዋል ባደረገው ጥረት የኦሮሚያ ክልል ጥሩ ትብብር እንዳደረገለት አስታውቋል።

በዚህም ምክንያት ከተጠረጠሩት 98 ግለሰቦች ውስጥ 44 ያህሉ በፌደራል የጸጥታ አካላት በቁጥጥር ስር መዋላቸውን አመላክተዋል።

በሶማሌ ክልል በፌደራል ፖሊስና መከላከያ 38 ግለሰቦች የተጠረጠሩ ሲሆን ከነዚህም ውስጥ 29 ያህሉ የእስር ትዕዛዝ ወጥቶባቸው በቁጥጥር ስር እንዲውሉ ቢወሰንም በቁጥጥር ስር የዋሉት ግን 5 ብቻ መሆናቸው ታውቋል።

የሶማሌ ክልል መስተዳድር በግብረ ሃይሉ ውሳኔ ላይ ይህ ዘገባ እስከተጠናቀረበት ጊዜ ድረስ ይፋዊ ምላሽ አልሰጠም።

ይህ በእንዲህ እንዳለ በግጭቱ ምክንያት ተፈናቅለው በመጠለያ ጣቢያዎች የሚኖሩ ዜጎች በከፍተኛ ስቃይ ላይ እንዳሉና በዚህም ምክንያት ከፍተኛ የስነ ልቦና ችግር እንደደረሰባቸው የፌደራል የአደጋ ስጋትና ስራ አመራር ኮሚሽን አስታውቋል።

ከቀያቸው የተፈናቀሉት ዜጎች ከመጠለያ ጣቢያ መውጣትና ልጆቻቸውን ወደ ትምህርት ቤት መላክ እንደሚፈልጉ ኮሚሽኑ አክሎ ገልጿል።

አቶ ሃይለማርያም ደሳለኝ ለፓርላማ ባቀረቡት እቅድ በቀጣይ ወራት ልዩ ትኩረት በመስጠት ተፈናቃዮችን ወደ ቀድሞ ቦታቸው መመለስ እንደሆነ ተናግረው ነበር።