የራያ ህዝብ የማንነትና የራስ አስተዳደር ጥያቄ ጊዚያዊ አስተባባሪ ኮሚቴ መሰረተ

የራያ ህዝብ የማንነትና የራስ አስተዳደር ጥያቄ ጊዚያዊ አስተባባሪ ኮሚቴ መሰረተ
( ኢሳት ዜና ሃምሌ 9 ቀን 2010 ዓ/ም ) ኮሚቴው ለኢሳት በላከው መግለጫ፣ የራያ ህዝብ ማንነቱ እውቅና እንዲያገኝ እና መሰረታዊ የሆኑት ሰብኣዊና ዲሞክራሲያዊ መብቶቹን እንዲከበሩ፣ የራያ ህዝብ ራሱ በሚፈቅደዉ መልኩ ተደረጅቶ ራሱን በራሱ እንዲያስተደደር ብሎም ፖለቲካዊና ምጣኔ ሀብታዊ መብቶቹ እንዲከበሩለት፣የራያ ህዝብ ከታሪካዊ፣ ስንልቦናዊና ባህለዊ ትስስር እንዲሁም ከማህበራዊ መስተጋብር አንጻር ከወሎ ህዝብ ጋር የተቆራኘ በመሆኑ፣ባጠቃላይም ደግሞ አማራ ክልል ዉስጥ ኦሮሞ፣ አገዉ፣ አርጎባ፣ እና ሌሎችም ብሄረሰቦች የሚኖሩበትና አካታች በመሆኑ የሰብአዊና ዲሞክራሲያዊ መብቱ ተከብሮለት፣በልዩ ዞን በአማራ ክልል የሚተዳደርበትን ሁኔታ ለመፍጠር እንዲሁም ራይኛ፤አማርኛና ኦሮምኛ የስራና የትምህርት ቋንቋ እንዲሆኑ ለማስቻል አልሞ እንደሚንቀሳቀስ አስታውቋል።
የራያ ህዝብ የማንነትና ራስን በራስ የማስተዳደር መብት አስከባሪ ምክር ቤት አቶ አገዘዉ ህዳሩን ሰብሳቢ፣ አቶ ጌታቸዉ ደሳለን ጸኃፊ እና ሌሎችንም 40 ሰዎች በተለያዩ የሃላፊነት ቦታዎች በመመደብ ኮሚቴውን ይፋ አድርጓል።