የመላው ኢትዮጵያ አንድነት ድርጅት፤“ሰላማዊ ትግሉም እየተበላሸ እና ወደ አላስፈላጊ ጫፍ እየተገፋ ነው” አለ

ሐምሌ ፮ (ስድስት) ቀን ፳፻፬ ዓ/ም

ኢሳት ዜና:-የአመራር አባሉ በጥይት ተደብድቦ የተገደለበት  የመላው ኢትዮጵያ አንድነት ድርጅት፤“ሰላማዊ ትግሉም እየተበላሸ እና ወደ አላስፈላጊ ጫፍ እየተገፋ ነው” አለ።

”የዳኝነት ሥርዓቱም  ቅጥ ባጣ መልኩ በኢህአዴግ  አመራር የሚሽከረከር አሻንጉሊት ሆኗል” ሲልም  መኢአድ የፍትህ ስርዓቱን አጥብቆ ኮንኗል።

ድርጅቱ ትናንት በሰጠው ጋዜጣዊ መግለጫ፤  በርካታ አመራሮቹና አባላቱ   ያለምንም ጥፋታቸው በኢህአዴግ ካድሬዎችና ታጣቂዎች  ሰብዓዊ ክብራቸው እየተገፈፈ እና ዲሞክራሲያዊ መብታቸው እየተጨፈለቀ እንደሚገኝ  አመልክቷል።

በተለይ በ አማራ ክልል የተለያዩ ዞኖች ውስጥ የሚገኙ አመራሮቹ  በግፍ እየተያዙ ወደ ወህኒ እየተወረወሩ መሆናቸውን የጠቀሰው መኢአድ፤ በሽብርተኝነት ህግ ሽፋን እየተፈፀመ ባለው ግፍ  ሰላማዊ ትግሉ እየተበላሸ እና ወደ ጠርዝ እየተገፋ እንደሆነ ገልጿል ።

የድርጅቱ ጸሀፊ አቶ ተስፋዬ ታሪኩ ትናንት ለጋዜጠኞች እንደተናገሩት፤ወጣት መልዴ እምቢአለ የተባለ የምስራቅ ጉጃም ዞን የደጀን ወረዳ ወኪልና የመኢአድ ወጣት ምክር ቤት ሥራ አስፈፃሚ አባል፤ ግንቦት 1 ቀን 2004 ዓ.ም በገዥው ፓርቲ ታጣቂዎች በጥይት ተደብድቦ ተገድሏል።

ቴዎድሮስ አያሌው የተባለ የሰሜን ወሎ  ዞን የ መኢአድ  አደራጅ ደግሞ –  ባለፈው ግንቦት ወር ከወልዲያ ከተማ  ተይዞ አዲስ አበባ ከመጣ በሁዋላ  የሀሰት ክስ ተመስርቶበት-  አቶ ተስፋዬ እንዳሉት-በህግ ሳይሆን በመመሪያ በሚሠራው ፍርድ ቤት የ 10 ዓመት እስራት ተፈርዶበት ወህኒ ወርዷል ።

በምዕራብ ጎጃም ዞን ፣በባህር ዳር እና  በሰሜን ወሎ በርካታ የወረዳ እና የዞን አመራሮች  በግፍ እየተያዙ መታሰራቸውንም  አቶ ተስፋዬ በዝርዝር አመልክተዋል።

”የዳኝነት ሥርዓቱ ቅጥ ባጣ መልኩ በኢህአዴግ  አመራር የሚሽከረከር አሻንጉሊት ሆኗል” ያሉት አቶ ተስፋዬ፤ በነ አንዷለም አራጌ መዝገብ በተከሰሱ የተቃዋሚ ፓርቲ አመራሮች እና ጋዜጠኞች ላይ  በቅርቡ የተሰጠው ብይንም ሆነ የችሎቱ ሂደት ይህንኑ ሀቅ ያረጋገጠ እንደሆነ ተናግረዋል።

የጸረ-ሽብር ህጉ በከፋ መልኩ እየተተረጎመ ብዙዎች ወደ ወህኒ እየተጋዙ ነው ያሉት አቶ ተስፋዬ፤በዚህም ሳቢያ  ዜጎች በህገ -መንግስቱ አንቀጽ 29 ላይ የሰፈረው ሀሳብን በነፃነት የመግለፅ መብታቸውን እንደተነጠቁ አመልክተዋል።

“የጸረ-ሽብር ህጉ ፤በህገ-መንግስቱ የተቀመጡ መብቶችን ሙሉ በሙሉ መጨፍለቂያ መሳሪያ ሆኗል”ሲሉም ጸሀፊው አክለዋል።

የኢትዮጵያ የፌዴራል ከፍተኛው ፍርድ ቤት፤  በነ አንዷለም አራጌ መዝገብ የፈጠራ የሽብርተኝነት ክስ  በተመሰረተባቸው የፖለቲካ ፓርቲ አመራሮችና ጋዜጠኞች ላይ ዛሬ ማርፈጃውን  ከ8 ዓመት እስከ እድሜ ልክ የሚደርስ ጽኑ እስራት መፍረዱ  ይታወቃል።

የእድሜ ልክ እስራት ከተፈረደባቸው  አራት ተከሳሾች  መካከል ፤ቀደም ሲል የሞት ፍርድ የተላለፈባቸው የግንቦት ሰባት ለፍትህ ለነፃነትና ለዲሞክራሲ ንቅናቄ ሊቀ-መንበር ዶክተር ብርሀኑ ነጋ አንዱ ናቸው።

ዶክተር ብርሀኑ በዚሁ ክሳቸው ዙሪያ ከቀናት በፊት ከኢሳት ጋር ቃለ-ምልልስ ሲያደርጉ፤  የፍትህ ሥርዓቱ   ለኢህአዴግ እንደ አንድ የመግደያ መሳሪያ በሚያገለግልበት መልክ መዋቀሩን ጠቅሰዋል።

ዶክተር ብርሀኑ ፤ይህ ወቅት፤  በኢትዮጵያ ታሪክ- ፍርድ ቤትና ዳኝነት እጅግ የተዋረዱበት ጊዜ መሆኑን ባብራሩበት በዚሁ ቃለ-ምልልሳቸው ፤አቶ መለስንና አቶ በረከትን፦”  የፍትህ ሥርዓቱን ለመግደል የሠራችሁት ሥራ ስለተሳካላችሁ እንኳን ደስ ያላችሁ!”ሲሏቸው ተደምጠዋል።

___________________________________________________________________________________________________________________________________________________

ESAT is the first independent Ethiopian satellite service tasked to produce accurate and balanced news and information, as well as other entertainment, sports and cultural programming created for and by Ethiopians.

ESAT is committed to the highest standards of broadcast journalism and programming and will strive to provide an outlet of expression to all segments of the diverse Ethiopian community worldwide