የሎሬት ጸጋዬ ገብረመድህን የጥናትና ምርምር ማዕከል ሊቋቋም ነው

(ኢሳት ዲሲ–ጥር 30/2011)በሎሬት ጸጋዬ ገብረመድህን ስም የጥናትና ምርምር ማዕከል ሊቋቋም መሆኑ ተገለጸ።

አምቦ ዩኒቨርስቲ ሎሬት ጸጋዬን በአርአያነት የሚያሳይና ለትውልድ ተምሳሌት በሚሆን መልኩ ማዕከሉን ለማቋቋም በዝግጅት ላይ መሆኑን አስታውቋል።

ማዕከሉ የሚቋቋመው በሎሬት ጸጋዬ ገብረመድህን የትወልድ ስፍራ መሆኑም ተገልጿል።

በሎሬት ፀጋዬ ገብረመድህን የስነ ፅሁፍ ስራዎች ላይ ምርምር ማድረግ እና እንደ ሎሬት ፀጋዬ ያሉ ምሁራንን ለማፍራት የሚያስችል ማዕከል ይሆናል ተብሏል።

በስነጽሁፍ ስራቸው ሁሌም የሚነሱት ሎሬት ጸጋዬ ገብረመድህን የስነጽሁፍ ፍቅር ያደረባቸው የ1ኛ ደረጃ ትምህርት ቤት ተማሪ እያሉ እንደነበርም የሕይወት ታሪካቸው ያስረዳል።

ሎሬት ፀጋዬ በርካታ ግጥሞችን እና የስነ ፅሁፍ፣የቲያትርና ዘፈኖችን ህይወታቸው እስካለፈበት 1998 ድረስ ማበርከታቸውም ታውቋል።

ሎሬት ፀጋዬ ገብረመድህን የተወለዱት በ1928 ዓ.ም አምቦ አካባቢ ቦዳ ተብላ በምትታውቅ ስፍራ ነው ።