የህወሀት አባላት የሆኑ ከፍተኛ የመንግስት ባለስልጣናት አሜሪካ በመምጣት ከትግራይ ተወላጆች ጋር ብቻ ሊመክሩ ነው

ታህሳስ ፲፮ (አስራ ስድስት) ቀን ፳፻፭ ዓ/ም

ኢሳት ዜና:-ምክትል የውጪ ጉዳይ ሚኒስትር ዶክተር  ደብረ-ጽዮን ገብረሚካኤል፣ የውጪ ጉዳይ ሚኒስትር ቴዎድሮስ አድሀኖም እና አቶ አባይ ወልዱ በመጪው ጥር ወር አሜሪካ በመምጣት  ስለ ኢትዮጵያ ወቅታዊ ጉዳይ ከትግራይ ተወላጆች ጋር ብቻ እንደሚመክሩ ተመለከተ።

የመንግስት ከፍተኛ ባለስልጣናቱ በ ኢትዮጵያ  ፖለቲካዊ ጉዳይ ከትግራይ ተወላጆች ጋር እንዲመካከሩ መድረኩን ያመቻቸው የትግራይ ልማት ማህበር ነው።

ደ-ብረብርሀን ብሎግ እንደዘገበው የትግራይ ልማት ማህበር በዲያስፓራ  ራሱን የቻለ የትግራይ መንግስት እየፈጠረ ያለ  ድርጅት ነው።

አንድ የትግራይ ተወላጅ ወደ ውጪ አገር በሚመጣበት ጊዜ ወዲያው በመመዝገብ ታክስ እንደሚሰበስብ የጠቀሰው ብሎጉ፤ ማህበሩ  ከረዥም ጊዜ አንስቶ በዲያስፖራ የሚገኙ የትግራይ ተወላጆችን ከሌሎች ኢትዮጵያውያን ወንድሞቻቸው ለመለየት እየደከመ የሚገኝ ጽንፈኛ ማህበር መሆኑን ጠቁሟል።

ይህ ጽንፈኛ ማህበር ከኢትዮጵያዊነት ይልቅ የትግራይ ብሄርተኝነትን ለማስፋፋት  እየተንቀሳቀሰ መሆኑን በማውሳትም፤ በመጪው ጥር ወር ወደ አሜሪካ የሚመጡት ከፍተኛ የመንግስት ባለስልጣናት በ አገር ጉዳይ ከትግራይ ተወላጆች ጋር ብቻ እንዲሰበሰቡ የግብዣ ጥሪ ያቀረበውና ፕሮግራሙን ያዘጋጀውም ይኸው የትግራይ ልማት ማህበር መሆኑን አመልክቷል።

በሚኒሶታና አካባቢው የሚኒሩ የትግራይ ተወላጆች በተደጋጋሚ ባወጧቸው መግለጫዎች ፦የመንግስት ባለስልጣናት  ወደ ወጪ አገር ሲመጡ የትግራይ ተወላጆች ጋር ብቻ ስብሰባ ማድረጋቸውን በማውገዝ፤ የህወሀት መሪዎች  የትግራይን ህዝብ ከሌላው የኢትዮጵያ ህዝብ ጋር ለመለያዬት ከሚከተሉት ጠባብ  የጎሰኝነት መንገድ እንዲታረሙ ማሻሰባቸው ይታወሳል።