ወደ ኬንያ የሚሰደዱ ኢትዮጵያውያን ቁጥር መጨመሩ ተገለጸ

(ኢሳት ዲሲ–መጋቢት 18/2010) በሞያሌ የተፈጸመውን ግድያ ተከትሎ ወደ ኬንያ የሚሰደዱ ኢትዮጵያውያን ቁጥር መጨመሩን አለም አቀፉ ቀይ መስቀል አስታወቀ።

መንግስት ስደተኞቹ እየተመለሱ መሆናቸውን ቢገልጽም አለም አቀፉ ቀይ መስቀል ትላንት እንዳስታወቀው በየቀኑ 500 ሰዎች እየተሰደዱ ኬንያ በመግባት ላይ ይገኛሉ።

ችግሩ በተፈጠረ በመጀመሪያዎቹ ሶስት ቀናት 8 ሺ 200 ኢትዮጵያውያን መሰደዳቸውን ያስታወሰው አለም አቀፉ ቀይ መስቀል በመጪዎቹ 3 ቀናት ቁጥሩ ወደ 15ሺ እንደሚያሻቅብም አስታውቋል።

የቀንድና የጋማ ከብቶችም በተመሳሳይ መሰደዳቸው ተመልክቷል።

የተባበሩት መንግስታት የስደተኞች ጉዳይ ከፍተኛ ኮሚሽን፣ የኬንያ ቀይ መስቀልና የስደተኞች ጉዳይ ጽሕፈት ቤት ባደረጉት ምዝገባ በመጋቢት ወር ብቻ ከሞያሌ ግድያ ጋር በተያያዘ ድንበር አቋርጠው ኬንያ የገቡ ኢትዮጵያውያን ቁጥር እስካለፈው ሳምንት 10ሺ 557 ደርሷል።

አሁንም በየቀኑ 100 ቤተሰቦች ማለትም በትንሹ 500 ያህል ሰዎች ድንበር አቋርጠው ኬንያ በመግባት ላይ መሆናቸውን በሰብአዊ ቀውስ ሪፖርቱ ላይ ተመልክቷል።

በየቀኑ 500 ያህል ሰዎች መሰደዳቸው በተገለጸበት በአሁኑ ወቅት በሚቀጥሉት ሶስት ቀናት የስደተኞቹ ቁጥር ወደ 15 ሺ እንደሚያሻቅብም አለምአቀፉ ቀይ መስቀል አስታውቋል።

አንዳንድ ስደተኞች የቤት እንስሳትን ጭምር ይዘው መሰደዳቸውም ይፋ ሆኗል።

በዚህም 600 ግመሎች፣2ሺ852 ላሞችና በሬዎች፣700 በግና ፍየሎች እንዲሁም 55 አህዮችም በተመሳሳይ ድንበር ተሻግረው ኬንያ መግባታቸው ታውቋል።

የአለምአቀፉን ቀይ መስቀል እንዳስታውቀው ባለፉት 15 ቀናት ኬንያ ከገቡት ኢትዮጵያውያን  ወስጥ 615 ነፍሰጡሮች ሲሆኑ 940ዎቹ ደግሞ አራስ እናቶች መሆናቸው ተመልክቷል።

እድሜያቸው ከ5 አመት በታች የሆኑት ሕጻናት ቁጥር ደግሞ 1 ሺ 478 መሆኑ ታውቋል።

125 ሕጻናት ደግሞ ወላጅም ሆነ አሳዳጊ ሳይኖራቸው መሰደዳቸውን ከሪፖርቱ መረዳት ተችሏል።

176 አዛውንቶችም ከተሰደዱት ውስጥ መሆናቸው ታውቋል።

የሞያሌውን ግድያ ተከትሎ በተፈጠረው ቀውስ ለደህንነታቸው ሰግተው የተሰደዱ ኢትዮጵያውያንን ለመደገፍ አለምአቀፉ ቀይ መስቀል ለሶስት ወራት የማቋቋሚያ ድጋፍ ጥሪ አቅርቧል።

እንደ አውሮፓውያኑ አቆጣጠር እስከ ሰኔ 23/2018 ድረስ የሚያስፈልጉትን ወጪ ዝርዝሮችም ይፋ አድርጓል።

በየቀኑ 100 ቤተሰቦች ማለትም 500 ያህል ሰዎች የሚሰደዱበት የሞያሌው ቀውስ የ13 ሰዎች መገደልን ተከትሎ የመጣ መሆኑን አለምአቀፉ ቀይ መስቀል አስታውቋል።

በመከላከያ ሰራዊት ከተገደሉት 13 ሰዎች በተጨማሪ 20 ሰዎች መቁሰላቸውን እንዲሁም 16 ደግሞ መሰወራቸውን አስታውቋል።