ወደ ኢትዮጵያ ሄደው ዘመዶቻቸውን ለመጠየቅ የፈለጉ ኢትዮጵያውያን ቪዛ እየተከለከሉ ነው

ግንቦት ፲፫ (አስራ ሦስት) ቀን ፳፻፬ ዓ/ም

ኢሳት ዜና:-ወደ  ኢትዮጵያ ሄደው ዘመዶቻቸውን ለመጠየቅ የፈለጉ በርካታ ኢትዮጵያውያን፦”የግንቦት 7 አባላት ናችሁ” እየተባሉ በየ አገራቱ ባሉት የኢትዮጵያ ኤምባሲዎች እየተከለከሉ ነው።

በቤልጂዬም የምትኖር እና ስሟን መግለጽ ያልፈለገች አንዲት ኢትዮጵያዊ ሰሞኑን ወደ አገሯ አቅንታ ዘመዶቿን ለመጠየቅ ብትፈልግም፤በብራሰልስ የሚገኘው የ ኢትዮጵያ ኤምባሲ ፦”የግንቦት ሰባት አባል  ስለሆንሽ ቪዛ አንሰጥሽም” በማለት ከልክሏታል።

ኤምባሲው  ለአክቲቪስቷ የግንቦት ሰባት አባልነት የጠቀሰውና ያቀረበው ማስረጃ  በተለያዩ ጊዜያት ኢትዮጵያውያን ባካሄዷቸው የተቃውሞ ሰልፎች ላይ መሳተፏን ነው።

እንዲሁም  በፍራንክፈርት፣ በዋሽንግተን ዲሲ እና በሌሎች የ አውሮፓ እና የአሜሪካ ከተሞች የሚኖሩ በርካታ ኢትዮጵያውያን ወደ አገር ቤት ለመሄድ ፈልገው ከየኤምባሲዎች  ተመሣሳይ ምላሽ ተሰጥቷቸው ቪዛ መከልከላቸውን ተናግረዋል።

የአቶ መለስ መንግስት ፦”የተቃውሞ ሰልፍ ማድረግ ህገ-መንግስታዊ መብት ነው” የሚል ህገ መንግስት ያረቀቀና ያጸደቀ ቢሆንም፤በተግባር እየተከተለ ያለው አገዛዝ፦”ንጉስ አይከሰስ፤ሰማይ አይታረስ” በሚል ያረጀ ብሂል የሚመራ  እንደሆነ ብዙዎች ይስማማሉ።

ፕሮፌሰር መስፍን ወልደማርያም፦”የ ኢትዮጵያ ህገ-መንግስት የተፃፈበትን ወረቀት ያህል ዋጋ አላወጣም”ማለታቸው አይዘነጋም።

___________________________________________________________________________________________________________________________________________________

ESAT is the first independent Ethiopian satellite service tasked to produce accurate and balanced news and information, as well as other entertainment, sports and cultural programming created for and by Ethiopians.

ESAT is committed to the highest standards of broadcast journalism and programming and will strive to provide an outlet of expression to all segments of the diverse Ethiopian community worldwide