ከፍተኛ ቁጥር ያለው ወታደር በወልድያ ባሉ ከተሞች ተሰማራ

(ኢሳት ዜና–ሕዳር 25/2010)

በወልዲያ ትላንት የተጀመረው የህዝብ ተቃውሞ ወደ ሌሎች አካባቢዎች መዛመቱን ተከትሎ የህወሃት መንግስት ከፍተኛ ቁጥር ያለው ወታደር በየከተሞቹ ማስገባቱ ተገለጸ።
በወልዲያ፣ ሀይቅ፣ ቆቦ መውጪያና መግቢያ ላይ በርካታ ወታደሮች የሚገኙ ሲሆን የሚወጣና የሚገባ ተሽከርካሪ እያስቆሙ እንደሚፈትሹ የደረሰን መረጃ አመልክቷል።
በሀይቅ ከተማ ታግተው ያሉት የሰላም ባስ አውቶቡሶችን ለማስለቀቅ የህወሃት ወታደሮች በሄሊኮፕተር መግባታቸውን ተከትሎም በሀይቅ ከተማ ውጥረት መንገሱ ይነገራል።
በትላንቱ ህዝባዊ ተቃውሞ ከስርዓቱ ጋር ግኑኝነት ያላቸው ግለሰቦች ንብረቶች ላይ ርምጃ መወሰዱ የሚታወስ ነው።
ከትግራይ ወደተለያዩ የኢትዮጵያ ከተሞች የሚጓጓዙ የሲሚንቶና የብረታብረት ምርቶች ከትላንት ጀምሮ ቆመዋል።
በወልዲያ ከተነሳው ተቃውሞ ጋር በተያያዘ በትግራይና አማራ ክልሎች ወሰን አካባቢዎች በተፈጠረው ውጥረት የተነሳ ተሽከርካሪዎች መንቀሳቀስ እንዳልቻሉ ይነገራል።
የመሶቦ ሲሚንቶ ምርቶች ከትላንት አንስቶ ከትግራይ ክልል መውጣት ያልቻሉ መሆናቸውም ተገልጿል።
ቆቦን ጨምሮ በሁለቱ ክልሎች አዋሳኝ በሆኑ አካባቢዎች የትግራይ ሚሊሻዎች የፌደራል ፖሊስ ትጥቅ ዩኒፎርም ለብሰው የተሰማሩ ሲሆን ከአማራ ልዩ ሃይል ጸጥታ የማስከበር ሃላፊነት መነጠቁን የደረሰን መረጃ ያመለክታል።
የወልዲያ ግጭት መነሻ የሆነውና በመቀሌ ቡድን ደጋፊዎች የተሰነዘሩት ስድቦች ያስቆጣቸው የአማራ ልዩ ሃይል አባላት ወገኖቻችን ላይ አንተኩስም የሚል ተቃውሞ ማሰማታቸውን ተከትሎ የህወሀት መንግስት እምነት በማጣቱ በተወሰኑ የአማራ አካባቢዎች የትግራይን ሚሊሻዎች በፌደራል ፖሊስ ዩኒፎርም እንዲሰማሩ ማድረጉ ታውቋል።
በዋናነትም በእነዚህ የአማራ አካባቢዎች የሚኖሩ የትግራይ ባለሃብቶችን የንግድ ቦታዎች ለመጠበቅ እንደሆነም ከምንጮች ዘገባ ለመረዳት ተችሏል።
ዛሬ ወልዲያ ጸጥ ረጭ ብላለች። ትምህርት ቤቶች የንግድ ቦታዎች መስሪያ ቤቶች ተዘግተዋል። የህወሀት አጋዚ ወታደሮች በየመንደሩና በየመንገድ መጋጠሚያ የአጋዚ ወታደሮች የተመደቡ ሲሆን ያገኙትን ወጣት እየያዙ ወደእስር ቤት በመውሰድ ላይ መሆናቸውን ከአካባቢው ከደረሰን መረጃ ለማወቅ ተችሏል።
በትላንትናው ተቃውሞ ከተገደሉት መሃል የአንድ መምህር የቀብር ስነስርዓት የተፈጸመ ሲሆን በወቅቱም የህወሀት መንግስት ላይ ያነጣጠሩ የተቃውሞ መልዕክቶች መሰማታቸው ተገልጿል።
በወልዲያ፣ ሀይቅ፣ ቆቦ መውጪያና መግቢያ ላይ በርካታ ወታደሮች የሚገኙ ሲሆን የሚወጣና የሚገባ ተሽከርካሪ እያስቆሙ እንደሚፈትሹ የደረሰን መረጃ አመልክቷል።
በሀይቅ ከተማ ታግተው ያሉት የሰላም ባስ አውቶቡሶችን ለማስለቀቅ የህወሀት ወታደሮች በሄሊኮፕተር መግባታቸውን ተከትሎም በሀይቅ ከተማ ውጥረት መንገሱ ይነገራል።
በአላማጣና በቆቦ የአማራ ተወላጆች ላይ የሚደርሰው እንግልት የትላንቱን የወልዲያ ተቃውሞ ተከትሎ የተባባሰ ሲሆን በአላማጣ የአንድ የወልዲያ ተወላጅ ሚኒባስ ተሽከርካሪ በትግራይ ታጣቂዎች እንዲወድም መደረጉ ታውቋል።
በመቀሌም በተመሳሳይ አማራው ላይ ያነጣጠረ ጥቃት የተፈጸመ ሲሆን ባንክ ቤቶችና የኢንሹራንስ ድርጅቶች ህንጻዎች መስታወቶቻቸው መሰባበሩን የደረሰን ዜና አመልክቷል።
በትላንቱ ህዝባዊ ተቃውሞ ከስርዓቱ ጋር ግኑኝነት ያላቸው ግለሰቦች ንብረቶች ላይ ርምጃ መወሰዱ የሚታወስ ነው።
በወልዲያ ህንጻዎች ላይ ጥቃት ተሰንዝሯል። የአጋዚ ወታደሮችን ሲያመላልስ የነበረ ተሽከርካሪም እንዲቃጠል ተደርጓል።
የህወሀት መንግስት በወሎ በተለያዩ ከተሞች የተነሳውን ተቃውሞ ለመቆጣጠር ከሰሜን ዕዝ ወደ ከተሞች ወታደሮችን ያስገባ ሲሆን ከአንዳንድ ቦታዎችም ሃይል በማንቀሳቀስ በወልዲያ፣ ቆቦ፣ ሀይቅ፣ አላማጣ ማስፈሩም ተመልክቷል።
በኢትዮጵያ የሚካሄዱ ተቃውሞችንና የህወሃት መንግስትን የአጸፋ ርምጃ የሚከታተሉ የፖለቲካ ታዛቢዎች እንደሚገልጹት በተነጣጠለ መልኩ የሚነሳው የህዝብ ተቃውሞ ለስርዓቱ ወታድሮቹን ከአንድድ ቦታ ወደሌላ ለማንቀሳቀስ እድል ሰጥቶታል።
በአንድ ጊዜ በሁሉም ቦታዎች የህዝብ እምቢተኝነት ቢቀሰቀስ ያለውን ሰራዊት ለማንቀሳቀስ የሚቸገር በመሆኑ ስርዓቱ የመውደቅ አደጋ ይገጥመዋል ሲሉም የፖለቲካው ታዛቢዎች ይገልጻሉ።
በተያያዘ ዜና በወልዲያ ውሃ ከጠጡ በኋላ በርካታ ሰዎች ሆስፒታል መግባታቸው ተሰምቷል።
ውሃው በንጽህና ጉድለት ይመረዝ ወይም በሌላ ምክንያት ግን የታወቀ ነገር የለም።
የኢሳት ምንጮች እንደገለጹት ዛሬ ውሃውን ጠጥተው ሆስፒታል የገቡ ሰዎች በተመሳሳይ የህመም ስሜት ውስጥ ናቸው።
ይህን በተመለከተ ኢሳት ዝርዝር መረጃ እንዳገኘ የሚያቀርብ ይሆናል።