ከስልጣን የተወገደው የህወሃት ስራ አስፈጻሚ ኮሚቴ ራሱን ወደ ጥገኛ ገዢ መደብ የማሸጋገር አዝማሚያ ተጠናውቶት ነበር ተባለ

(ኢሳት ዜና–ሕዳር 21/2010)በአባይ ወልዱ ሲመራ የነበረው የህወሃት ስራ አስፈጻሚ ኮሚቴ ራሱን ወደ ጥገኛ ገዢ መደብ የማሸጋገር አዝማሚያ ተጠናውቶት እንደነበር የሕወሃት ማዕከላዊ ኮሚቴ በአቋም መግለጫው አስታወቀ።
ስራ አስፈጻሚው የውሸት ሪፖርት ሲያወጣ እንደነበርም ተመልክቷል።

በትግራይ ማህበረሰብ ዘንድ የአድዋ ተወላጆች ስልጣኑን ሙሉ ለሙሉ ተቆጣጠሩት የሚል አስተያየት በሰፊው በመደመጥ ላይ ነው።

ለተራዘሙ ቀናት በመቀሌ ግምገማ ተቀምጦ የነበረው የሕወሃት ማዕከላዊ ኮሚቴ ህዳር 21/2010 ድርጅታዊ የአቋም መግለጫ አውጥቷል።

በዚህ መግለጫው ማዕከላዊ ኮሚቴው ስር ነቀል ግምገማ በማካሄድ የእርምት ርምጃና የአመራር ሽግሽግ በማድረግ ማጠናቀቁን አስታውቋል።

የአቋም መግለጫው ካለፉት ጥቂት አመታት ወዲህ ስትራቴጂካዊ አመራሩ እየተዳከመ ተልዕኮውን ለመወጣት የሚያስችለው ቁመና፣አመለካከትና አደረጃጀት ተሸርሽሯል ይላል።

ይህንን ቁመና ይዞ የሕወሃት መስመርንም ሆነ የመለስ ሌጋሲን ለማስቀጠል የሚቻልበት ሁኔታ እንደሌለ በግልጽ ማየቱን ገልጿል።

በአቶ አባይ ወልዱ ሊቀመንበርነት ሲመራ የነበረው የስራ አስፈጻሚ ኮሚቴ ከገባበት የችግር አዙሪት ውስጥ መውጣት አቅቶት ሲዳክር መቆየቱን እንዳረጋገጠ ማዕከላዊ ኮሚቴው በመግለጫው አስታውቋል።

ስራ አስፈጻሚው የሃሳብና የተግባር አንድነት የጎደለው፣ጸረ-ዲሞክራሲ ተግባርና አስተሳሰብ ውስጥ በስፋት የተነከረ፣በተልዕኮ ዙሪያ በመተጋገልና በመርሕ ላይ የተመሰረተ አመራር የማይሰጥ፣ህዝብና አላማን ከማስቀደም ይልቅ የራሱን ክብርና ጥቅም የሚያስቀድም ብሎታል።

አያይዞም ስራ አስፈጻሚ ኮሚቴው ለሕዝብ ያለው ወገንተኝነት እየተሸረሸረ፣ከአገልጋይነት ይልቅ ራሱን እንደ ተገልጋይ እየቆጠረ፣መዋቅራዊ ለውጥ በሚያመጡ ስኬታማ የሕዝብ ዙሪያ መለስ እንቅስቃሴ ከመጠመድ ይልቅ በተደማሪ ለውጦች የሚረካና በውሸት ሪፖርት ራሱን መሸለም የሚያቅተው አመራር እየሆነ በአጠቃላይ ራሱን ወደ ጥገኛ ገዢ መደብ የማሸጋገር አዝማሚያ የተጠናወተው በማለት መግለጫው ፈርጆታል።

ማዕከላዊ ኮሚቴው ያካሄደው የአመራር ለውጥ በህወሃት ውስጥ በስፋት ይስተዋል የነበረውን የሃሳብና የተግባር አንድነት ችግር ስር ነቀል በሆነ መልኩ ለመፍታት ያስችላል ቢልም በትግራይ ህዝብ ዘንድ እየተነገረ ያለው በተቃራኒው መሆኑን ለማወቅ ተችሏል።

በተለይም በመገናኛ ብዙሃንና በማህበራዊ ድረ-ገጾች ንቁ ተሳታፊ የሆኑ የትግራይ ተወላጆች አዲስ የተመደበውን ስራ አስፈጻሚ የአድዋ ተወላጆች መቆጣጠራቸውን በማስረጃ በማቅረብ ላይ ናቸው።

የቀድሞ የአረና ትግራይ በኋላም የአንድነት ፓርቲ አመራር አባል የነበረው አስራት አብርሃም በሀገር ቤት በሚታተም ጋዜጣ ላይ “የሕወሃት ፖለቲካ የአድዋ ፖለቲካ ነው።በአድዋ ቤተሰቦች የሚሽከረከር ፖለቲካ ነው።ከበፊትም ቢሆን ተንቤን፣እንደርታ፣ሽሬና ራያ ከፖለቲካ ስልጣን የተገለሉ ናቸው”በማለት አስተያየቱን ሰጥቷል።

በማህበራዊ መድረክ ከተሰራጩ የትግራይ ተወላጆች አስተያየት መረዳት እንደተቻለው አሁን የፓርቲውን ስራ አስፈጻሚነት ከያዙት 9 ሰዎች ሊቀመንበሩን ዶክተር ደብረጺዮንና ምክትላቸው ወይዘሮ ፈትለወርቅ ገብረእግዜብሔርን ጨምሮ 7ቱ የአድዋ ተወላጆች ናቸው።