ከሀላፊነታቸው ተነስተው የነበሩት ጄነራል ሞላ ተመለሱ

ህዳር ፲፯ (አስራ አምት) ቀን ፳፻፬ ዓ/ም

ኢሳት ዜና:- በኢትዮጵያ መከላከያ ሰራዊት ውስጥ ብወዛ ለማድረግ ከላይ የተጀመረው እንቅስቃሴ ሳንካ እንደገጠመው የመከላከያ ምንጮች ገለጡ።

በሜጀር ጀኔራል ማህሪ ዘውዴ እንዲተኩ የተወሰነባቸው የአየር ሀይል አዛዥ ሜጀር ጄነራል ሞላ ሀይለ ማሪያም ተመልሰው ስፍራቸውን መያዛቸውን የአየር ሀይል ምንጮች ገለጸዋል።

የቀድሞው ጠቅላይ ሚኒስትር መለስ ዜናዊ ከዚህ አለም በሞት መለየታቸው ለህዝብ ከመገለጹ በፊት በመከላከያ ሰራዊት ውስጥ ሲካሄድ የቆየውን ግምገማ ተከትሎ የአመራር ሽግሽግ ለማድረግ የተጀመረው ሙከራ ከመነሻው ሳንካ ገጥሞታል።

የአየር ሀይል አዛዥ ሜጀር ጄነራል ሞላ ሀይለማሪያም በሜጀር ጄነራል መሀሪ ዘውዴ እንዲተኩ ከተወሰነ በሆላ በህውሀት ውስጥ በተፈጠረ መሳሳብ ሂደቱ መቀልበሱ ተሰምቶል።እንዲነሱ ተወስኖባቸው የነበረው ሜጀር ጄነራል ሞላ ሀይለማሪያምም ሆኑ ሜጀር ጀነራል መሀሪ ዘውዴ ሁለቱም የህውሀት ታጋዮች እንደነበሩም ለማወቅ ተችሎል።

በስራቱ ውስጥ ወጥ የሆነ አመራር አለመኖሩና ተሰሚ የሆነ ግለሰብ ነጥሮ አለመውጣቱ እንዲሁም በህውሀት ውስጥ የአውራጃ ስሜት እየጎላ መምጣቱ ለችግሩ በምክንያትነት እየተጠቀሰ ይገኛል።