ኦነግና ኦፌኮ ጥምረት ለመመስረት ድርድር ጀመሩ

ኦነግና ኦፌኮ ጥምረት ለመመስረት ድርድር ጀመሩ
( ኢሳት ዜና ነሐሴ 24 ቀን 2010 ዓ/ም ) የኦሮሞ ነጻነት ግንባር እና የኦሮሞ ፌደራሊስት ኮንግረስ ጥምረት እንደሚፈጥሩ የታወቀው፣ አስመራ የሚገኘውን በአቶ ዳውድ ኢብሳ የሚመራውን የኦነግ አመራር ቡድን ለመቀበል ስለሚደረገው ዝግጅት ጋዜጣዊ መግለጫ በሰጡበት ወቅት ነው።
ኦነግ የትጥቅ ትግሉን በማቆም በሰላማዊ መንገድ ለመታገል እንደወሰነ፣ በቅርቡ ከኦሮምያ ክልል ፕሬዚዳንት ለማ መገርሳ ጋር ባደረገው ውይይት አስታውቆ ነበር።
በሌላ በኩል መቀመጫቸውን ኤርትራ ያደረጉና ለአመታት በኢህአዴግ ላይ የትጥቅ ትግል ሲያደርጉ የነበሩት የተቃዋሚ ድርጅቶች ትግላቸውን በሰላማዊ መንገድ ለማካሄድ በመወሰን ሁሉም ወደ ኢትዮጵያ እንዲመለሱ ለማድረግ ጥረቶች ቀጥለዋል። የደህንነት ሚኒስትሩ ወደ አስመራ በማቅናት ከትግራይ ህዝብ ዴሞክራሲያዊ ንቅናቄ ጋር ውይይት አድርገዋል። ሁሉም ታጣቂ ሃይሎች ወደ ኢትዮጵያ ሲገቡ፣ በኢትዮጵያ መንግስት ላይ የሚካሄድ የትጥቅ ትግል አይኖርም። የዶ/ር አብይ መንግስት የወሰደው የሃይል አማራጭን የመዝጋት እርምጃ፣ በአገሪቱ ውስጥ ዘላቂ ሰላምን ለማስፈን እየረዳ መሆኑን በርካታ የፖለቲካ ተንታኞች ይናገራሉ።
በኤርትራ ምድር የነበሩት የአርበኞች ግንቦት7 የሰራዊት አባላት በሚቀጥሉት ቀናት ወደ ኢትዮጵያ ይገባሉ ተብሎ ይጠበቃል።