እነ አቶ በቀለ ገርባ የ6 ወራት ተጨማሪ እስራት ተወሰነባቸው

(ኢሳት ዲሲ–ጥር 3/2010)

አቶ በቀለ ገርባን ጨምሮ የኦሮሞ ፌደራሊስት ኮንግረስ አመራር አባላት የሆኑ ተከሳሾች ፍርድ ቤትን ደፍራችኋል በሚል የ6 ወራት ተጨማሪ የእስራት ቅጣት ተወሰነባቸው።
ውሳኔው የተለለፈው የፌደራሉ ከፍተኛው ፍርድ ቤት 4ኛ ወንጀል ችሎት የራሱን ውሳኔ በመሻር ጠቅላይ ሚኒስትር ሃይለማርያም ደሳለኝን ጨምሮ ከፍተኛ የመንግስት ባለስልጣናት ለምስክርነት አይቀርቡም ሲል ውሳኔ ማሳለፉን በመቃወማቸው ነው።


የፌደራሉ ከፍተኛ ፍርድቤት ከዚህ ቀደም በሰጠው ውሳኔ ጠቅላይ ሚኒስትር ሃይለማርያም ደሳለኝን ጨምሮ 4 ከፍተኛ የመንግስት ባለስልጣናት የተከሳሾች መከላከያ ምስክር ሆነው እንዲቀርቡ ወስኖ ነበር።
በመከላከያ ምስክርነት እንዲቀርቡ ታዘው የነበሩት ሌሎች ባለስልጣናትም አፈ ጉባኤ አባዱላ ገመዳ፣የኦሮሚያ ፕሬዝዳንት ለማ መገርሳ፣የኦሕዴድ ጽህፈት ቤት ሃላፊ ዶክተር አብይ አህመድና ጫልቱ ናኒ በኦሮሚያ ክልል የለገዳዴ ከተማ ከንቲባ ናቸው።
በኦሮሞ ፌደራሊስት ኮንግረስ ከፍተኛ አመራር አባላት አቶ በቀለ ገርባና ሌሎች ተከሳሾች በመከላከያ ምስክርነት እንዲቀርቡ ትዕዛዝ የተሰጠባቸው እነዚሁ ከፍተኛ ባለስልጣናት ለ3 ጊዜ ያህል ፍርድቤት እንዲቀርቡ ቢታዘዙም አንዳቸውም አልተገኙም።
ከዚሁ ጋር ተያይዞም የጠቅላይ ሚኒስትር ጽህፈት ቤት አቶ ሃይለማርያም ደሳለኝ ፍርድቤት ተጠርተው ያልተገኙት ስራ ስለሚበዛባቸው ነው በሚል ደብዳቤ መጻፉ ይታወሳል።
የኦሮሚያው ፕሬዝዳንት አቶ ለማ መገርሳና የኦሕዴድ ጽህፈት ቤት ሃላፊ ዶክተር አብይ አሕመድ ግን በወቅታዊ የሀገር ጉዳይ ላይ ስብሰባ ላይ መሆናቸውን ገልጸው የቀጠሮ ቀኑ እንዲቀየርላቸው ጠይቀው ነበር።–በድርጅቱ ማዕከላዊ ኮሚቴ ጽሕፈት ቤት በኩል።
ይህም ሆኖ ግን የፌደራሉ ከፍተኛ ፍርድ ቤት 4ኛ ወንጀል ችሎት በዛሬ ውሎው የራሱን ውሳኔ በመሻር ሁሉም ከፍተኛ ባለስልጣናት በረባም ባረባም ጉዳይ ፍርድቤት መጠራት የለባቸውም በሚል ለምስክርነት እንዳይቀርቡ ወስኗል።
ባልስልጣናቱ የሕዝብ ስራ ስላለባቸው ፍርድ ቤት ለመቅረብ ጊዜ የላቸውም ነው ያለው 4ኛ ወንጀል ችሎት አዲስ ስታንዳርድ እንደዘገበው።
እናም በዚህ የተበሳጩት አቶ በቀለ ገርባ፣ደጀኔ ጣፋ፣አዲሱ ቡላላና ጉርሜሳ አያኖ የፍርድ ቤቱ ውሳኔ ህግን ያልተከተለ ነው ሲሉ ተቃውመውታል።
ተከሳሶቹ ተቃውሞአቸውን በዝማሬ በመግለጻቸውም ፍርድ ቤቱ አቶ በቀለ ገርባን ጨምሮ አራቱ ተከሳሾች ፍርድ ቤት በመድፈር ወንጀል የ6 ወራት እስራት እንዲቀጡ ወስኖባቸዋል።
ለእነ አቶ በቀለ ገርባ ተቃውሞ በጭብጨባ ድጋፋቸውን የሰጡትና በአርበኞች ግንቦት ሰባት ሰበብ በአሸባሪነት የተከሰሱ ሌሎች 3 ተከሳሾችም ለምን እንደዚህ እንዳደረጉ በፍርድ ቤቱ ተጠይቀው ነበር።
እነሱም “ለወንድሞቻችን ድጋፍ ለመስጠት ነው”በማለታቸው ፍርድ ቤት ደፍራችኋል ተብለው በ3 ወራት እስራት እንዲቀጡ ነው የተወሰነባቸው።
በዋናው ክሳቸው ሳይፈረድባቸው በእስር ላይ ሆነው ሌላ እስራት የተፈረደባቸው እነዚሁ ተከሳሾች በፍርድ ቤቱ ላይ እምነት ስለሌለን ከእንግዲህ ወደ ችሎት አንመጣም፣ከፈለጋችሁም አካላችንን ጎትታችሁ ታመጡ እንደሆነ እናያለን ሲሉ በፍርድ ቤቱ ላይ አፊዘዋል።
በሕወሃት የሚመራው የኢትዮጵያ አገዛዝ የፖለቲካ ምህዳሩን ለማስፋት የተወሰኑ እስረኞችን እለቃለሁ በማለት ለሕዝብ ቃል ቢገባም እስካሁን ተግባራዊ አልሆነም።