እቴጌ ጣይቱ ብጡል ሃውልት ሊቆምላቸው ነው

(ኢሳት ዲሲ–ነሐሴ 23/2010)ለእቴጌ ጣይቱ ብጡል በአዲስ አበባ ሃውልት ሊቆምላቸው ነው።

ነገ በአዲስ አበባ አድዋ ድልድይ አካባቢ የሃውልቱ የመሰረት ድንጋይ እንደሚጣልም የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር አስታውቋል።

በአስተዳደሩ ቱሪዝምና ባህል ቢሮ የወጣው ደብዳቤ ላይ እንደተመለከተው የአዲስ አበባ ከተማ ምክትል ከንቲባ ኢንጅነር ታከለ ኡማና አርቲስት አለምጸሀይ ወዳጆ የመሰረት ድንጋዩን ያኖራሉ።

አዲስ አበባን የቆረቆሩት እቴጌ ጣይቱ ብርሃን ዘ ኢትዮጵያ በአድዋ ጦርነት በነበራቸው የተለየ ሚና ታሪክ ሁሌም ሲዘክራቸው ይኖራል ብላለች አርቲስ አለምጸሐይ ወዳጆ።

ለዓመታት የእቴጌ ጣይቱን ሃውልት በቆረቆሯት ከተማ ለመትከል ስትጎተጉት የከረመችው አርቲስት አለምጸሀይ ወዳጆ ህልሟ እውን የሚሆነው ይህ ሃውልት ቆሞ ስታይ መሆኑን ተናግራለች።

ከ25 ዓመታት በኋላ ትላንት ወደ ሀገሯ የገባችው አርቲስ አለምጸሀይ ወዳጆ በአቀባበል ፕሮግራሙ ላይም ይህን ህልሟን አንስታ መንግስትም ሆነ ህዝቡ እንዲተባበራት መጠየቋ የሚታወስ ነው።

ኢንጅነር ታከለ ኡማ በተገኙበት ነገ የሚካሄደውን የእቴጌ ጣይቱ ሀውልት የመሰረት ድንጋይ የማኖር ስነስርዓት ላይ ህዝቡ ተገኝቶ ድጋፉን እንዲያሳይም ተጠይቋል።