ኢትዮጵያ፣ ግብጽና ሱዳን በአባይ ጉዳይ ላይ ተስማሙ ተባለ

(ኢሳት ዲሲ–ግንቦት 10/2010)ኢትዮጵያ ግብጽና ሱዳን በአባይ ጉዳይ ላይ ስምምነት ላይ መድረሳቸው ተነገረ።

በሶስቱ ሃገራት መካከል ጊዜያዊ ስምምነት በመደረሱም በመካከላቸው የነበረው ውጥረት ረግቧል ተብሏል።

በጋራ ሚንስትሮቻቸው አማካኝነት ስምምነት ላይ የደረሱት ኢትዮጵያ፣ ግብጽ እና ሱዳን የግድቡን ውሃ አሞላል በተመለከተ ጉዳዩን የሚከታተል የሳይንቲስቶች ቡድን ጥናት እንዲያደርግ ነው ።

ኢትዮጵያ ግብጽና ሱዳን በአባይ ግድብ ግንባታ ጉዳይ ላይ በርካታ ውይይቶች ሲያደርጉ የነበረ ቢሆንም ስምምነት ለይ ሳይደርሱ ቆይተዋል።

በተለይ ደግሞ ከግድብ ግንባታ ጋር በተያያዘ ኢትዮጵያ የተወሰነውን ሀይል ውሀ ለመሙላት እንቅስቃሴ ስትጀምር ከግብጽ በኩል ከፈተኛ ተቃውሞ ሲያጋጥማት ቆይቷል።

በመሆኑም ውይይቱ እንዲስተጓጎል ምክንያት ሆኖ ነበር ግብጽ የግድቡን ግንባታ የአባይን ውሀ መጠን ይቀንሳል ባይ ነች እናም የውሀው መቀነስ ጥቅሜን ይጎዳል በሚል ስታደናቅፍ ቆይታለች ነው የተባለው።

ግብጽ በ1959 ከሱዳን ጋር በነበራት ስምምነት የአባይን ውሀ ለራሷ በሚጠቅም መንገድ መደራደር ትፈልጋለች ።

ኢትዮጵያና ሱዳን ግን ይህንን የግብጽ ሀሳብ አይቀበሉም በዚህ ምክኒያት የሶስትዮሹ ስምምነት ሲደነቃቀፍ ቢቆይም ሲስቱም ሀገራት በአዲስ አበባ ባካሄዱት ውይይት ጊዜያዊ ስምምነት ላይ መድረሳቸው ተነግሯል።

ግድቡን በተመለከተ ገለልተኛ የፈረሳይ ኩባንያዎች እያጠኑት ቢሆንም የግብጽ ኢትዮጵያና የሱዳን የውጪ ጉዳይ የመስኖና የደህንነት መስሪያ ቤቶች በአዲስ አበባ ባካሄዱት ውይይት የግድቡን ውሀ ለመሙላት በሳይንቲስቶች እንዲጠና ስምምነት ላይ ደርሰዋል።

ይህም ስምምነት በመካከላቸው የነበረውን አለመግባባትና አታካሮ ለጊዜውም ቢሆን እንዲቀዘቅዝ አድርጎታል ተብሏል።

የአባይ ግድብ ግንባታ 6 ቢሊየን ዶላር ይወጣበታል ተብሎ ይገመታል።