ኢትዮጵያውያን አንድ ሆነን በመስራት ሃገራችንን እናበልጽግ ተባለ

(ኢሳት ዲሲ–ጥቅምት 21/2011)ጠቅላይ ሚኒስትር አብይ አሕመድ በብሔር ሳንከፋፈልና አንድ ሆነን በመስራት ሃገራችንን እናበልጽግ ሲሉ ጥሪ አቅርቡ።

በጀርመን ፍራንክፈርት ከኢትዮጵያውያን ጋር በስታዲየም ውስጥ የታደሙት ጠቅላይ ሚኒስትር አብይ አሕመድ በርትተን በመስራት የበለጸገችውን የነገን ኢትዮጵያን መገንባታችን አይቀርም ሲሉ ተስፋቸውን ገልጸዋል።

ለዚሁም ምቹ ሁኔታን ለመፍጠር ብቁ ሰዎችን በመመደብ የፍትህና የዲሞክራሲ ተቋማትን የማሻሻል ርምጃ እየተወሰደ ነው ብለዋል።

ጠቅላይ ሚኒስትር አብይ አሕመድ ከተለያዩ የአውሮፓ ሃገራት ተሰባስበው በጀርመን ፍራንክፈርት ለታደሙ ኢትዮጵያውያን የሃገርን በጋራ እናበልጽግ ጥሪ ደጋግመው አቅርበዋል።

ዶክተር አብይ እንዳሉት ለነገው ትውልድ የምትሆንና የበለጸገች ኢትዮጵያን ለመገንባት ፈታኝ ስራ ከሁሉም ዜጎች ፊት ተደቅኗል።

እናም ኢትዮጵያዊነትን ከስሜት በዘለለ በስራ የምንገልጽበት ወቅት ላይ ነን ብለዋል።

እንደ ጠቅላይ ሚኒስትር ዶክተር አብይ ገለጻ ዛሬንና ነገን ጥሩ ማድረግ የሚቻለው ስለትላንት በመነታረክ መሆን የለበትም።

ኢትዮጵያም ደክማ ይሆናል እንጂ አልሞተችም ሲሉ ስለ ነገ ያላቸውን ተስፋ ነው የገለጹት።

ጠቅላይ ሚኒስትር አብይ አህመድ ስለ ኢትዮጵያ ያላቸውን ተስፋ ሲገልጹም በሃገሪቱ ስደት ቀርቶ ጎብኝዎች ፍልሰት ቀርቶ ተቀባይ እንሆናለን ብለዋል።