ኢትዮጵያውያን ልዩነቶቻቸውን አስወግደው በጋራ ለመንቀሳቀስ መወሰናቸውን አስታወቁ

(ኢሳት ዜና–ሕዳር 8/2010)በአሜሪካ ሚኒሶታ ግዛት የሚኖሩና በተለያዩ ማህበረሰቦች የተደራጁ ኢትዮጵያውያን ልዩነቶቻቸውን አስወግደው በሀገራቸው ጉዳይ ላይ በጋራ ለመንቀሳቀስ መወሰናቸውን አስታወቁ።

በዚህም በግጭት የተፈናቀሉ ዜጎችን ለመታደግ የገንዘብ ማሰባሰቢያ ፕሮግራም ማዘጋጀታቸውን አስታውቀዋል።

ኢትዮጵያውያኑ በጋራ ያስተባበሩትና ለተፈናቃዮች መደገፊያ የሚሆን የገቢ ማሰባሰቢያ የሙዚቃ ዝግጅት ነገ በሴንትፖል ሚኒሶታ እንደሚካሄድ ታውቋል።

በአሜሪካ ሚኒሶታ ግዛት የሚኖሩትና በተለያዩ ማህበረሰቦች ተደራጅተውና ሳይደራጁ ሲንቀሳቀሱ የነበሩት ኢትዮጵያውያን በሀገራቸው ጉዳይ ላይ በአንድነት ለመንቀሳቀስ ወደ 6 ወራት የፈጀ ውይይት ማድረጋቸው ተመልክቷል።

በዚህም በተፈጠረው ቅርርብና ትብብር የሃይማኖት መሪዎች፣አባገዳዎች እንዲሁም አዛውንቶች በተገኙበት ባለፈው መስከረም መጨረሻ ሰፊ ውይይት አካሂደው የጋራ መግለጫ አውጥተዋል።

ለወገኖቻቸው ያላቸውን አጋርነትም አረጋግጠዋል።

ኢትዮጵያውያን በአካባቢና በብሔር እንዲሁም የእምነት ግጭት እንዳይፈጥሩ፣ግጭት ለመፍጠር የሚንቀሳቀሱትንም እንዲመክቱ በጋራ ጥሪ አቅርበዋል።

በሚኒሶታ የሚኖርቱ ኢትዮጵያውያን በግጭት የተፈናቀሉትን ለመርዳት በገቡት ቃል መሰረት ነገ ጥቅምት 18/2017 የሙዚቃ ፕሮግራም ማዘጋጀታቸውን አስታውቀዋል።

ከቀትር በኋላ 4pm ተጀምሮ ለሊት 2AM በሚጠናቀቀው የሙዚቃና የገቢ ማሰባሰቢያ ዝግጅት በሚኒያፖሊስና በሴንት ፖል ከተሞች የሚኖሩት ኢትዮጵያውያን እንዲገኙ ጥሪ አቅርበዋል።