ኢህአዴግ ቀጣዩን ምርጫ ካሸነፈ አዲስ ተሿሚዎቹ ጠቅላይ ሚኒስትሮች በስልጣናቸው ይቀጥላሉ ሢሉ አቶ በረከት ስምዖን ተናገሩ

መስከረም ፯ (ሰባት) ቀን ፳፻፭ ዓ/ም

ኢሳት ዜና:-የመንግስት ቃል አቀባይ አቶ በረከት ይህን ያሉት፤ የኢህአዴግ ምክር ቤት ቅዳሜ ዕለት ሊቀ-መንበሩን እና ምክትል ሊቀ-መንበሩን መምረጡን ተከትሎ ከኢህአዴግ ጽህፈት ቤት ሀላፊው ከአቶ ሬድዋን ሁሴን ጋር በሂልተን በሰጡት ጋዜጣዊ መግለጫ ነው።

ቀደም ሲል የህወሀቱን አቶ ስብሀት ነጋን ጨምሮ በርካታ ሰዎች ተጠባባቂ ጠቅላይ ሚኒስትር ሆኖ የሚመረጠው ሰው ሹመቱ የሚቆየው እስከ ቀጣዩ ምርጫ እንደሆነ እና ከዚያ ኢህአዴግ በምርጫው ካሸነፈ በፓርላማ ቋሚ ጠቅላይ ሚኒስትሩን እንደሚሾም በተደጋጋሚ ሲናገሩ መቆየታቸው ይታወሳል።

አቶ በረከት በሂልተን በሰጡት መግለጫ ግን ኢህአዴግ ቀጣዩን ምርጫ ሲያሸንፍ አሁን የተመረጡት አቶ ሀይለማርያም ደሳለኝ እና አቶ ደመቀ መኮነን በያዙት ቦታቸው እንደሚቀጥሉ ነው ከወዲሁ የተናገሩት።

አቶ በረከት የአቶ መለስ ሞት በኢትዮጵያ ቴሌቪዥን በተነገረ በዚያኑ ቀን በፍጥነት በሰጡት ጋዜጣዊ መግለጫ፦” አቶ ሀይለማርያም ጠቅላይ ሚኒስትር በመሆን አቶ መለስን ተክተው ይሠራሉ” በማለት   መናገራቸው በህወሀት አባላት ዘንድ ከፍ ያለ ተቃውሞ ገጥሞት እንደነበር መዘገቡ አይዘነጋም።

ቅሬታው ባልበረደበት ሁኔታ ነው አቶ በረከት በአሁኑ መግለጫቸው፦”ኢህአዴግ ቀጣዩን ምርጫ ካሸነፈ አዲሶቹ የድርጅቱ ሊቃነ-መናብርት፤ ዋና እና ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትሮች ሆነው ይቀጥላሉ” ያሉት።

የኢሳት ዘጋቢዎች ከአገር ቤት ያሰባሰቧቸው መረጃዎች እንደሚያሳዩት፤ከቀናት በፊት በአመዛኙ ከህወሀት የሆኑ መኮንኖች በጀነራልነት የተሾሙ ቢሆንም፤ህወሀት ከ 21 ዓመታት በሁዋላ ከጠቅላይ ሚኒስትርነት ወንበር ላይ ሙሉ በሙሉ መገለሉ ያልተዋጠላቸው ህወሀቶች፤ድርጅታቸው በብዙ ዘርፎች የደከመበት ደረጃ ላይ እንደሚገኝ ማውራት ጀምረዋል። ጉዳዩን በቅርብ የሚከታተለው ዘጋቢያችን እንዳለው ደግሞ ህወሀት የቀድሞ ሀይሉን ይዞ ለመቀጠል ሊቸግረው ይችላል።

አቶ በረከት በሂልተኑ መግለጫቸው ህወሀት በአቶ መለስ ምትክ ሊቀ-መንበሩን ገና አልመረጠም ሲሉም ተናግረዋል።

ያለ ዋና ሊቀ-መንበር ከሁለት ወራት በላይ የቆየው ህወሀት እስካሁንም መሪውን መተካት ያልቻለው በውስጡ በተፈጠረ የስልጣን ሽኩቻ ምክንያት እንደሆነ በተደጋጋሚ ይነገራል።ኢሳት የውስጥ ምንጮችን በመጥቀስ እንደዘገበው አቶ አባይ ወልዱ የህወሀት ሊቀመንበር ሆነው ተመርጠዋል፡

አንጋፋው የህወሀት መስራች አቶ ስብሀት ነጋ በአቶ መለስ ሞት ማግስት፤-“መለስ ፤ህወሀትንም ጭምር ነው ገድሎት የሞተው” በማለት የቀድሞ የድርጅቱን ታጋዮች ሲቀሰቅሱ እንደነበር መዘገቡ ይታወሳል።

___________________________________________________________________________________________________________________________________________________________________________

ESAT is the first independent Ethiopian satellite service tasked to produce accurate and balanced news and information, as well as other entertainment, sports and cultural programming created for and by Ethiopians.

ESAT is committed to the highest standards of broadcast journalism and programming and will strive to provide an outlet of expression to all segments of the diverse Ethiopian community worldwide