አቶ አባዱላ ገመዳ እና አቶ ግርማ ብሩ ጡረታ ወጡ

(ኢሳት ዲሲ–ሰኔ 1/2010) አቶ አባዱላ ገመዳ እና አቶ ግርማ ብሩ ጡረታ እንዲወጡ ተወሰነባቸው ።

አቶ ግርማ ብሩ በሚኒስትርነት እና በአምባሳደርነት 27 ዓመታተ ሥርዓቱን ሲያገለግሉ ፣አቶ አባዱላ ገመዳ ደግሞ በጦር አዛዥነት፣በአፈጉባኤነት እና በክልል ፕሬዝዳንትነት ሰርተዋል።

ጠቅላይ ሚኒስትር አብይ አህመድ ሁለቱን  የኦህዴድ የቀድሞ መሪዎች በጡረታ ያሰናበቱት በትናትናው ዕለት ነው።

ኦሕዴድ በመጋቢት 1982 ሰሜን ሸዋ ደራ ላይ በሕወሃቱ የደህንነት ሃላፊ አቶ ክንፈ ገብረመድህን አማካኝነት እንደተመሰረተ ሲገለጽ ቆይቷል።

በሕወሃት አስተባባሪነት ደራ ላይ ኦሕዴድን ከመሰረቱት ሰዎች አንዱ የሆኑት አቶ አባዱላ ገመዳ የደርግ መንግስት ሲወገድ በመከላከያ ሰራዊቱ ውስጥ ተመደቡ።

የኢሕአዴግ የመከላከያ ሰራዊት ወደ ኢትዮጵያ መከላከያ ሰራዊትነት ሲቀየርና ማዕረግ ሲታደል የጄኔራልነት ማዕረግ ከደረሳቸው አንዱ አባዱላ ነበሩ።

በ1993 ሕዝባዊ ወያኔ ሃርነት ትግራይ ለሁለት ሲሰነጠቅ የአቶ መለስን ቡድን ለማዳን መለዮአቸውን አስቀምጠው አቶ አባዱላ ሆኑ።

ቀጥሎም የኦሕዴድን አመራር በኋላም የክልሉን ፕሬዝዳንትነት የወሰዱት አቶ አባዱላ ገመዳ ከአቶ መለስ ቡድን ጋር አብረው ዘልቀዋል።

በ2002 የኦህዴዶ ማዕከላዊ ኮሚቴ አባዱላ ገመዳን የኦሕዴድ ሊቀመንበር አድርጎ መልሶ  ቢመርጥም፣ በአቶ መለስ ዜናዊ ትዕዛዝ ምርጫው ተሽሮ ኦሕዴዶች እንደገና አዳማ ላይ ተሰብስበው አቶ አለማየሁ አቶምሳን በሊቀመንበርነት መርጠዋል።

አቶ መለስ ዜናዊ ምክንያቱ ባልታወቀ ሁኔታ አቶ አባዱላ የኦሕዴድ ሊቀመንበር እንዳይሆኑ በግልጽ ጣልቃ ገብተው ውሳኔ ቢያስቀይሩም አቶ አባዱላ ገመዳ ግን ታማኝነታቸውን ሳያጓድሉ መቀጠላቸው ሲገለጽ ቆይቷል።

የአቶ አባዱላ ምርጫ ውጤት ተሽሮ አቶ አለማየሁ አቶምሳ እንዲመረጡ አቶ መለስ ሲወስኑ አሁን ከአቶ አባዱላ ጋር የተሰናበቱት አቶ ግርማ ብሩ ጭምር ለሕገወጡ የአቶ መለስ ትዕዛዝ ተገዢዎች ነበሩ።

በወቅቱ የኦሕዴድ ማዕከላዊ ኮሚቴ አባላት ከነበሩት ውስጥ የሰጠሁትን ድምጽ አልቀይርም ያሉት ብቸኛ ሰው ለማ መገርሳ እንደነበሩ “አዲስ ፎርቹን ጋዜጣ ካቀረበው ዘገባ ማስታወስ ተችሏል።

ከኦሮሚያ ክልል ፕሬዝዳንትነት ወደ ፌደራሉ መንግስት አፈ-ጉባኤነት የተሸጋገሩት አቶ አባዱላ ገመዳ ከወራት በፊት የሕዝቤ ክብር ተነካ ብለው መልቀቂያ ማቅረባቸው ይታወሳል።

በጥቂት ሳምንታት ውስጥ እንደገና ወደ ስራቸው የተመለሱት አቶ አባዱላ ገመዳ የአስቸኳይ ጊዜ አዋጁ የመጽደቅ ሒደትን ጨምሮ በተለያዩ ጉዳዮች ከለውጡ ሃይል በተቃራኒ ከሕወሃት ጎን ተሰልፈው መቆየታቸውም ተመልክቷል።

ጠቅላይ ሚኒስትር አብይ አሕመድ ወደ ኢሕአዴግ ሊቀመነበርነት እንዳይመጡ ከተንቀሳቀሱትና ለሕወሃት ታማኝነትን ሳያጓድሉ ቀጠሉ የሚባሉት አቶ አባዱላ ገመዳ የአቶ አብይ የደህንነት አማካሪ ሆነው መሾማቸው ብዙዎችን ያስገረመ ነበር።

ሆኖም የሹመት ድልድሉ ኢሕአዴግ ባቀረበው ግብረሃይል የተፈጸመ እንጂ በጠቅላይ ሚኒስትር አብይ ፍላጎት አይደለም የሚሉ አስተያየቶች በወቅቱ ተደምጠዋል።

አቶ አባዱላ ገመዳ ለአንድ ወር ያህል ብቻ የተቀመጡበትን የደህንነት አማካሪነት ሹመት ለቀው ትላንት በጡረታ ተሸኝተዋል።

የኦሮሚያ ክልል አሁን አልፎ አልፎ ከሚከሰቱ የብሔረሰብ ግጭቶችና መፈናቀል ጋር በተያያዘ አቶ አባዱላ ገመዳ ከሕወሃት የደህንነትና ወታደራዊ መዋቅር ጋር በትብብር እየሰሩና የራሳቸውንም የቀደመ መዋቅር ለዚህ ተግባር እያዋሉ ነው በሚል ይጠረጠራሉ።

ሌላው ትላንት በጡረታ የተሸኙት አቶ ግርማ ብሩ በደርግ ስርዓት የኢሰፓ አባል የነበሩና በደርግ ስርአት ውስጥ በዝቅተኛ የሃላፊነት ስፍራ ያገለገሉ መሆናቸው ተመልክቷል።

ኢሕአዴግ አዲስ አበባ ሲገባ የመከላከያ ምክትል ሚኒስትር በመሆን በአዲሱ መንግስት ውስጥ ድንገት ባለስልጣን ሆነው ብቅ ያሉት አቶ ግርማ ብሩ በስርአቱ ውስጥ በሙያቸው አዋቂ ከሚባሉ ጥቂት ግለሰቦች አንዱ ናቸው ።

ሆኖም ለሕወሃት መሪዎች ፍጹም ባላቸው ታማኝነትና አድርባይ ባህርይ ብዙዎች ይተቿቸዋል።

በቅርቡ ከአሜሪካ አምባሳደርነት የተነሱት አቶ ግርማ ብሩ በውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ውስጥ የሰሜን አሜሪካ ሀገራት አስተባባሪ የሚል ሹመት ተሰቷቸው ነበር።

በአዲሱ ሹመት ሶስት ወራትን ሳያስቆጥሩ ትላንት በጡረታ ተሰናብተዋል።

በቅርቡ አቶ ስብሃት ነጋ እና ዶ/ር ካሱ ኢላላን ጨምሮ ነባር የኢሕአዴግ አመራሮች በተመስሳይ በጡርታ መሰናበታቸው ይታወሳል።አቶ አባይ ጸሃዬ፣አቶ ቴዎድሮስ ሃጎስ እና አቶ ዘርዓይ አስገዶም ከነበሩበት ሃላፊነት መነሳታቸውም አይዘነጋም።