አቶ አባዱላ ገመዳ አሁንም በአፈጉባኤነታቸው መቀጠላቸው ታወቀ

(ኢሳት ዜና–ጥቅምት 2/2010) በሳምንቱ መጨረሻ ከፓርላማ አፈጉባኤነታቸው ለመልቀቅ ጥያቄ ማቅረባቸውን ያሳወቁት አቶ አባዱላ ገመዳ አሁንም በአፈጉባኤነታቸው መቀጠላቸው ታወቀ።

ዛሬ ጥቅምት 2/2010 የተሰየመውን ፓርላማ በአፈጉባኤነት መምራታቸውም ታውቋል።

አቶ አባዱላ ገመዳ በመሩት በዛሬው ስብሰባ ልዩ ልዩ አዋጆች ቀርበው ጸድቀዋል።

ፓርላማው ሰኞ ዕለት ስራ ሲጀምር በስብሰባው ማጠቃለያ ከመድረክ ጀርባ የምስጋናና የስንብት አሸኛኘት ከፓርላማ አባላትና ከሃይማኖት አባቶች እንደጠበቃቸው የተገለጸው አቶ አባዱላ ገመዳ ተመልሰው በፓርላማ ወንበራቸው መቀጠላቸው ግልጽ አልሆነም።

አቶ አባዱላ በመንበራቸው ላይ የቀጠሉት ለጊዜው ይሁን ለዘለቄታው ስለመሆኑ የታወቀ ነገር የለም።

በስራቸው ላይ የቀጠሉት በማግባባት ይሁን በማስገደድ ይህም ግልጽ አልሆነም።

አቶ አባዱላ ገመዳ መልቀቂያ ለማን እንዳቀረቡ አሁንም ግልጽ ሳይሆን የቀጠለ ሲሆን ራሳቸው ግን ለፓርላማውና ለድርጅታቸው ማስገባታቸውን መግለጻቸው ይታወሳል።

የመንግስት ቃል አቀባይ ዶክተር ነገሬ ሌንጮ ደግሞ መልቀቂያውን ያቀረቡት ለጠቅላይ ሚኒስትር ሃይለማርያም ደሳለኝና ለኦህዴድ ነው በማለት አቶ አባዱላ ከተናገሩት የተለየ መረጃ ሰጥተዋል።

የኢህአዴግ ጽህፈት ቤት ሃላፊ አቶ ሽፈራው ሽጉጤ አቶ አባዱላ ያቀረቡት መልቀቂያ የለም በማለት ለቪኦኤ መናገራቸውም ይታወሳል።

በሀገር ቤት የሚታተመውና በቀድሞው የሕወሃት ታጋይ በአቶ አማረ አረጋዊ የሚመራው ሪፖርተር ጋዜጣ ጥያቄው የቀረበው ለኢህዴግ ጽሕፈት ቤት ነው ማለቱ አይዘነጋም።–ጥያቄው ተቀባይነት ማግኘቱንም ዘግቧል።

ይህ በእንዲህ እንዳለም ሰኞ በተከፈተ ምክር ቤት ላይ ሌላ አስደናቂ ክስተት እንደነበርም ሪፖርተር ያወጣው መረጃ አመልክቷል።

እንደ ሪፖርቱ ከሆነም በሁለቱ ምክር ቤቶች አባላት ከሆኑት ከፍተኛ ባለስልጣናትና በአጠቃላይ ከ600 በላይ ከሚሆኑት የምክር ቤቶቹ አባላት አብዛኞቹ የሀገሪቱን ብሔራዊ መዝሙር ስንኞች አያውቋቸውም።

እናም ጉዳዩ ግራ ያጋባው የምክር ቤቱ ጽሕፈት ቤትም ብሔራዊ መዝሙሩን በወረቀት ላይ በማተም ስንኞቹን ከወረቀቱ ላይ እያዩ እንዲዘምሩ ማድረጉ ታውቋል።

ወረቀቱ የታደላቸው የምክር ቤቶቹ አባላትም ስንኞቹን ከወረቀት ላይ እያነበቡ ለመዘመርም ሲሳናቸው የተስተዋሉ መሆናቸውን የአይን እማኞች ተናግረዋል።