አቶ በረከት ስምኦን በቁጥጥር ስር ዋሉ

(ኢሳት ዲሲ–ጥር 15/2011)አቶ በረከት ስምኦን በቁጥጥር ስር ዋሉ።

የአማራ ክልል የጸረ ሙስና ኮሚሽን እንዳስታወቀው አቶ በረከት ስምኦን የታሰሩት በሌብነት ተጠርጥረው ነው።

የብአዴን አመራር አባል  የነበሩት አቶ ታደሰ ካሳም በተመሳሳይ ሰዓት ከመኖሪያ ቤታቸው መያዛቸውንና ወደ ባህርዳር መወሰዳቸው ታውቋል።

አቶ በረከት ስምኦንን ዛሬ ማለዳ አዲስ አበባ የሚገኘውን መኖሪያ ቤታቸውን የከበቡ የአማራ ክልል ፖሊሶች ወደ ባህርዳር  እንደወሰዷቸውም ታውቋል።

ባህርዳር 9ኛ ፖሊስ ጣቢያ ውስጥ ለምርመራ መታሰራቸውንም የቅርብ ምንጮች ገልጸዋል።

የብአዴን አመራር አባል  የነበሩት አቶ ታደሰ ካሳም በተመሳሳይ ሰዓት ከመኖሪያ ቤታቸው መያዛቸውንና እንደ አቶ በረከት ወደ ባህርዳር መወሰዳቸውን መረዳት ተችሏል።

አቶ በረከት ስምኦን የፌደራል ፖሊስ እንጂ የአማራ ክልል ፖሊስ ሊይዘኝ አይገባም በማለት ቢያንገራግሩም ፖሊሶቹ ጠንከር ሲሉባቸው ትዕዛዙን ተቀብለው መኪናው ውስጥ መግባታቸውን የቅርብ ምንጮች ገልጸዋል።

አቶ በረከት ስምኦን እና አቶ ታደሰ ካሳ ጥረት ከተባለው የብአዴን ኩባንያ ጋር በተያያዘ በፈጸሙት ምዝበራ ተጠርጥረው መታሰራቸውንም የአማራ ክልል ጸረ ሙስና ኮሚሽን ኮሚሽነር  አቶ ዝግአለ ገበየሁ ዛሬ ለመገናኛ ብዙሃን ገልጸዋል።

የብአዴን አመራር አባላት የሆኑት አቶ በረከት ስምኦን  እና አቶ ታደሰ ካሳ ከዚሁ ከተጠረጠሩበት ሌብነት ጋር በተያያዘ በነሐሴ ወር ከፓርቲው ማዕከላዊ ኮሚቴ አባልነት  መታገዳቸውም ይታወሳል።

የአቶ በረከትን መታሰር ተከትሎ የባህርዳር ነዋሪዎች በአደባባይ  ደስታቸውን እየገለጹ ሲሆን፣ፖርቹጋላዊቷ የአውሮፓ ፓርላማ አባል ወ/ሮ አና ጎሜዝም የአቶ በረከት መታሰር ለብዙዎች እፎይታ ነው ብለዋል።

በምርጫ 1997 የአውሮፓ ሕብረት የታዛቢዎች ቡድን መሪ የነበሩት አና ጎሜዝ በምርጫ 1997 በአዲስ አበባ ጎዳና ለፈሰሰው ደም ተጠያቂ ከሚያደርጓቸው የኢሕአዴግ  ባለስልጣናት አንዱ አቶ በረከት ስምኦን ናቸው።