አቶ በረከት ስምኦንና አቶ ታደሰ ካሳ ፍርድ ቤት ቀረቡ

(ኢሳት ዲሲ–የካቲት 15/2011)አቶ በረከት ስምኦንና አቶ ታደሰ ካሳ ለ3ኛ ጊዜ ዛሬ ፍርድ ቤት ቀረቡ።

በጥረት ኮርፖሬት ተፈፅሟል በተባለ የሀብት ምዝበራ የተጠረጠሩት አቶ በረከት ስምኦንና አቶ ታደሰ ካሳ ለሶስተኛ ጊዜ ፍርድ ቤት ሲቀርቡ ተጨማሪ የ14 ቀን ቀጠሮ ተጠይቆባቸዋል።

ፍርድ ቤቱ በጥያቀው ላይ ወሳኔ ለመስጠት ለ ሰኞ ቀጠሮ ሰጥቷል።

የአማራ ክልል ፀረ ሙስና ኮሚሽን አቃቢ ህግ ተጨማሪ ምርመራዎችን ለማድርግ የ14 ቀናት ጊዜ ቀጠሮ ጠይቋል።

አቃቤ ህጉ ዳሽን ቢራ ዲዮት ለተባለው የእንግሊዝ ኩባንያ የአክሲዮን ድርሻ የሸጠበትን 96 ሚሊዮን ዶላር የት እንዳደረሰው አልታወቀም ሲል እነ አቶ በረከትን ሲወነጅል እንደነበር ይታወሳል።

እነ በረከት ስምዖን እና ታደሰ ካሳ የጥረት አመራር በነበሩበት ጊዜ የኩባንያውን ሀብት በማባከንን በሌብነት ተጠርጥረው መታሰራቸው ይታወሳል።

የክልሉ ጸረ ሙስና አቃቤ ህግ ይ14 ቀን የጊዜ ቀጠሮ የጠየቀው የዳሽን ቢራ የሂሳብ ኦዲት አለመጠናቀቅ የጥረት ኮርፖሬት የአክሲዮን ሽያጭ ህጋዊነት በባለሙያ ማስፈትሽ ስላስለፈለገ ነው ብሏል።

ከዢህ ጋር በተያየዘም 2 ዋነኛ ምስክሮች ከሀገር ውጪ ስለሆኑ የሚመለሱበትን ቀን ታሳቢ በማድረግ ጥያቄው መቅረቡንአቃቤ ህግ  በምክንያትነት ገልጿል።

እነ አቶ በረከት ግን ኦዲቱ ባልተጠናቀቀ ጉዳይ ነው ወይ መዝብረዋል በሚል የተከሰስነው ሲሉ ፍርድ ቤቱን ጠይቀዋል ተብሏል።

ይህ ተገቢ አይደለም አቃቢ ህግ ሆን ብሎ እኛን በእስር ለማቆየት የሚያቀርበው ምክንያት ነው ሲሉም ተጨማሪ ይ 14 ቀን የምርመራ ጊዜውን ተቃውመዋል ።

ጉዳዩን እየተመለከተ ያለው ፍርድ ቤት ጉዳዩን መርምሮ ተጨማሪ የምርመራ ጊዜ ያስፈልጋል ወይ የሚለውን ለመወሰን ለመጪው ሰኞ ተለዋጭ ቀጠሮ ይዟል።

ይሕ በእንዲህ እንዳለም አቶ በረከት ስምዖን የእስር አያያዛቸውን በተመለከተ ጠባቂዎችን እያሰቸገሩ መሆናቸውን የኢሳት ምንጮች ገልጸዋል።

የታሰረነውም ሆነ ፍርድ አየተሰጠን ያለው በማህበራዊ ሚዲያ ሰለሆነ ይሕንን ለመከታተል እንድንችል ኢንተርኒት ይግብላን የሚሉት አቶ በረከት ጠባቂዎችን ኢሳት ምን አለ እያሉ መረጃ ለማግኘት እንደሚያስቸግሩ ለማወቅ ተችሏል።

አቶ በረከት ስምኦን እና አቶ ታደሰ ካሳ በአሁኑ ጊዤ የተፈቀደላቸው  ሬዲዮ ብቻ መሆኑም ምንጮች ገልጸዋል።