አርበኞች ግንቦት7 በሃረር ከተማ ስብሰባ እንዳያካሂድ ተከለከለ

አርበኞች ግንቦት7 በሃረር ከተማ ስብሰባ እንዳያካሂድ ተከለከለ
( ኢሳት ዜና ጥቅምት 02 ቀን 2011 ዓ/ም )ክልሉ ለድርጅቱ መስከረም 18 ቀን 2011 ዓም በጻፈው ደብዳቤ “ በጸጥታ ምክር ቤት ጉዳዩ ታይቶ በክልሉ ባለው ሃገራዊ ሁኔታ አንጻር ተገምግሞ የተጠየቀው ፍቃድ አለመፈቀዱን እንገልጻለን” ብሎአል።
ክልከላውን በማስመልከት ልክልሉ ም/ል ፕሬዚዳንት አቶ ጋቢሳ ተስፋዬና ለጸጥታ ክፍል ሃላፊው አቶ አበበ መብራቱ ስልክ በተደጋጋሚ ብንደውልም ሊመልሱልን አልቻሉም።
የአርበኞች ግንቦት7 የአመራር አባል የሆኑት አቶ አበበ ቦጋለ በሰጡን አስተያየት፣ ክልሉ የጣለው እገዳ የተጀመረውን ለውጥ የሚያጨልም ተደርጎ መታየት የለበትም ያሉ ሲሆን፣ አገሪቱ ሽግግር ላይ ስላለች አንዳንድ ቦታ ላይ ለውጡን ለመቀልበስ የሚፈልጉ ሃይሎች ሴራ መሆኑን በመረዳት ከክልሉ አስተዳደርና ከፌደራል መንግስቱ ጋር እየተነጋገርን አገር የማረጋጋት ስራ እንሰራለን ብለዋል።
ክልከላው በአርበኞች ግንቦት7 ላይ ብቻ ለምን ሆነ? ሌሎች ድርጅቶችስ ለምን አልተከለከሉም በማለት ለቀረበላቸው ጥያቄ፣ “ድርጅቱ የሚከተለው የፖለቲካ አስተሳሰብ ባለፉት 27 አመታት ሲራመድ ከነበረው አስተሳሰብ ጋር የተለዬ በመሆኑ የተፈጠረ ድንጋጤ” ሊሆን ይችላል ብለዋል።
አርበኞች ግንቦት 7 ቅዳሜ ጥር 3 በአዳማ የድጋፍና የውይይት ፕሮግራም እንደሚያካሂድ ታውቋል።