ናዋዝ ሸሪፍ የ10 አመት የእስር ትዕዛዝ ተላለፈባቸው

(ኢሳት ዲሲ–ሰኔ 29/2010) የቀድሞው የፓኪስታን ጠቅላይ ሚኒስትር ናዋዝ ሸሪፍ የ10 አመት የእስር ትዕዛዝ ተላለፈባቸው።

ፍርድ ቤቱ በቀድሞው ጠቅላይ ሚኒስትር ላይ ውሳኔውን ያሳለፈው ስልጣናቸውን አላግባብ በመጠቀም የሃገሪቱን ገንዘብ መዝብረዋል በሚል ነው።

ተዘረፈ በተባለው ገንዘብም በለንደን አራት የቅንጦት መኖሪያ ቤቶችን መግዛታቸውንና ከህዝብ በዘረፉት ገንዘብ የቅንጦት ኑሮ  እየመሩ ነው በሚል ፍርድ ቤቱ ማስረጃውን አቅርቧል።

ፍርድ ቤቱ በወንጀሉ ተባባሪ ናት ባላት የቀድሞ ጠቅላይ ሚኒስትር ናዋዝ ሸሮፍ ሴት ልጅ ላይም የ7 አመት እስራት ወስኗል።

የልጃቸው የትዳር አጋርም ለአንድ አመት ዘብጥያ እንዲወርድ ብይን ተላልፎበታል።

ናዋዝ ሸሪፍ ውሳኔውን የፖለቲካ ጣልቃ ገብነት አለበት ሲሉ አጣጥለውታል።

ናዋዝ ሸሪፍ ከሃገር በመዘበሩት ገንዘብ ልጆቻቸው በተለያዩ ሀገራት የብዙ ኩባንያ ባለቤቶች እንዲሆኑ አድርገዋል በሚል ወቀሳ ሲቀርብባቸው ቆይቷል።–ዘገባው የቢቢሲ ነው።