ተስፋ የወጣቶች ድርጅት በኢትዮጵያ በራሪ ወረቀቶ በተነ

(Sept. 17) የኢትዮጵያ ተስፋ ወጣቶች ድርጅት የተሰኘ አገር በቀል ስብስብ፤ በአዲስ አበባ በተለያዩ ስፍራዎች ከ25 ሺህ በላይ ቀስቃሽና ኢህአዴግ ሰራቸው የሚላቸውን ጥፋቶች የሚዘረዝሩ በራሪ ወረቀቶችን በተነ።
በተለይ ለኢሳት የደረሰው ዜና እንደሚያመለከተው፤ ድርጅቱ በአይነቱ የመጀመሪያ በሆነ መልኩ፤ በአዲስ አበባ በተለያዩ ስፍራዎች፤ የኢትዮጵያ ህዝብን ለትግል የሚቀሰቅሱ ወረቀቶችን መበተኑን አስታወቋል።
ከሌሎች ምንጮቻችን ማረጋገጥ እንደቻልነው በአዲስ አበባ በላፍቶ ክ/ከ በአዲሱ ገበያ፤ በኮልፌ፤ ፒያሳና፤ ሽሮ ሜዳ አካባቢ ወረቀቶች መበተናቸው ታውቋል።
የኢትዮጵያ ተስፋ ወጣቶች ድርጅት በበተነው አንደኛ ወረቀት ላይ የህወሀት ኢህአዴግ አገዛዝ በሀይማኖት ተቋማት ላይ ያደረሰውን ጣልቃገብነትና ጥፋት፤ በኑሮ ውድነት ረገድ ያለውን ችግር፤ የተለያዩ ብሄሮችን በማጋጨትና ከኖሩበት ቀዬ በማፈናቀል ያደረሰውን ጥፋት ዘርዝሯል።
ድርጅቱ ለመንግስት አካላት በተለይም ለፖሊስ፤ ለደህንነት፤ ለመከላከያ ሰራዊት ለቀበሌና ወረዳ ባለስልጣናት ህዝብን ከሚጎዳ ስራ እንዲታቀቡ ማስጠንቀቂያ አስተላልፏል።
ድርጅቱ በበተነው ሌላ ወረቀት ላይ በምርጫ 1997 የተገደሉና የቆሰሉ ሰዎችን እንዲሁም የሚያለቅሱ እናቶችን ምስሎች አስፍሮ፤ ጎን ለጎንም ኢህአዴግ አደረሰ የሚላቸውን በደሎች ዘርዝሯል።
የኢትዮጵያ ተስፋ ወጣቶች ድርጅት በቅርቡ ከተቋቋመው የነጻ ኢትዮጵያ ሰራዊት ንቅናቄ (ነኢሰን) የተገኘ የቅስቀሳ ወረቀትም የበተነ ሲሆን፤ ከነኢሰን በተገኘ ወረቀት ላይ በተለይ መከላከያ ሰራዊቱን የተመለከተና ጦር ሰራዊቱ ከህዝቡ ጎን እንዲቆም ጥሪ የሚያደርግ መልክእክት ማስፈሩ ታውቋል።