ባለፉት 10 አመታት በአዲስ አበባ የተገነባው ከአጼ ሚኒሊክ ጀምሮ ከተገነባው ይበልጣል ሲሉ አቶ ኩማ ደመቅሳ ተናገሩ

ህዳር ፲፱ (አስራ ዘጠኝ) ቀን ፳፻፭ ዓ/ም

ኢሳት ዜና:-ከንቲባው ይህን የተናገሩት  በቅርቡ የአዲስ አበባ 125ኛ አመት ክብረ በአል ሲጠናቀቅ ባደረጉት የመዝጊያ ንግግር ነው።

አቶ ኩማ ከተማዋን የቆረቆሩትን እና በከተማዋ ላይ አሻራቸውን ያሳረፉትን በሙሉ በማውገዝ የኢህአዴግን ስራ ለማሞካሸት ሞክረዋል።

በነገሥታቱ ዘመን የከተማዋ የመሬት ይዞታ ለመኳንንት፣ ለመሳፍንትና ለጦር አበጋዞች ተከፋፍሎ አብዛኛው የከተማዋ ነዋሪዎች ሲሰቃዩ እንደኖሩ፣ የከተማዋ ዕድገት ማስተር ፕላንን ያልተከተለ በመሆኑና በመኳንንቱና በመሳፍንቱ ግላዊ ፍላጐት ተወስኖ ቆይቷል ሲሉ ነው ከንቲባው የገለጹት።

ባለፉት አሥር ዓመታት  በከተማዋ በሁሉም መስኮች የተገኘው ውጤትና እየታየ ያለው ለውጥ፣ ከመቶ ዓመታት በላይ በከተማዋ ተሠርተው ከነበሩት ልማቶች በብዙ እጥፍ ይበልጣል በማለት ነው አቶ ኩማ የተናገሩት።

አዲሱ ምክትል ጠቅላይ ሚኒሰትርና የትምህርት ሚኒሰትሩ አቶ ደመቀ መኮንን ፣ ‹‹ነዋሪዎቿ በቀጥታ ተሳትፈው የዕድገት ምህዋር ውስጥ ገብታ የዓለም አቀፍና የአፍሪካ መዲና ሆና የወጣችው  ካለፉት ሁለት አሥርተ ዓመታት ወዲህ ነው፤›› በማለት የአቶ ኩማን ንግግር አጠናክረዋል፡፡

ከተማዋን የቆረቆሩት አጼ ሚኒሊክም ሆኑ እቴጌ ጠሐይቱ እንዲሁም አጼ ሀይለስላሴ በጊዜው በፈቀደላቸው ቴክኖሎጂና በነበራቸው የገንዘብ አቅም እና እውቀት ለአዲስ አበባ ማደግ ከፍተኛ አስተዋጽኦ ማድረጋቸውን የታሪክ ባለሙያዎች ይናገራሉ።

አጼ ሀይለስላሴ አፍሪካ አንድነት ድርጅትንና የአለም የኢኮኖሚ ኮሚሽን ጽህፈት ቤት አዲስ አበባ እንዲሆን የታገሉና አዲስ አበባ ዛሬ ላገኘችው አለማቀፍ ክብር ከፍተኛ አስተዋጽኦ  ማድረጋቸውን ድርሳናት ያወሳሉ።

የአቶ መለስ መንግስት በአዲስ አበባ ላይ ከፍተኛ መዋለ ንዋይ በማፍሰስ ከተማዋ እንድትለማ ያደረገው ከምርጫ 97 በሁዋላ በአዲስ አበባ የደረሰበትን ሽንፈት ተከትሎ መሆኑን ታዛቢዎች ይናገራሉ።

ያም ሆኖ በከተማዋ የሚኖሩ ነዋሪዎች አሁንም በመሰረተ ልማት አቅርቦት በተለይም በውሀና በመብራት እጦት በእጅጉ እየተማረሩ ነው። ቤታቸው እየፈረሰባቸው ያለ በቂ ካሳ መንገድ ላይ እንዲያድሩ የተደረጉትም ቁጥራቸው ቀላል አለመሆኑን ኢሳት በተደጋጋሚ ሲዘግብ ቆይቷል።

አቶ ኩማ በከተማዋ  የሚታየውን የመሬት ዝርፊያ ለማስቆም ሳይችሉ ኢህአዴግን ከነጋስታቱ ዘመን ጋር ለማወዳደር መቻላቸው ለትችት ዳርጎአቸዋል። አዲስ አበባ ከሌሎች የአፍሪካ አገሮች ጋር ስትነጻጸር አሁንም ሁላ የቀረች ከተማ ነች።