በግብጽ በተፈጸመ የቦምብ ጥቃት ቢያንስ 235 ሰዎች ተገደሉ

(ኢሳት ዜና–ሕዳር 15/2010)በግብጽ ሳይናይ ግዛት በአንድ መስጊድ ላይ በተፈጸመ የቦምብ ጥቃት ቢያንስ 235 ሰዎች ሲገደሉ 130 ሰዎች ቆስለዋል።

የሟቾቹም ሆነ በጥቃቱ የቆሰሉ ሰዎች ቁጥር ከዚህም በላይ ሊያሻቅብ እንደሚችል መረጃዎች ጠቁመዋል።

የሀገሪቱ ፕሬዝዳንት የሶስት ቀናት ብሔራዊ የሀዘን ቀንም አውጀዋል።

እስካሁንም ለጥቃቱ በይፋ ሃላፊነት የወሰደ አካል የለም ።

በግብጽ ሳይናይ ግዛት ዛሬ በአንድ መስጊድ ላይ በደረሰው የሽብር ጥቃት ይህ ዜና እስከተጠናቀረበት ሰአት ድረስ ቢያንስ 235 ሰዎች ሲገደሉ 130 ሰዎች ላይ ደግሞ ጉዳት ደርሷል።

አርብ እኩለ ቀን ላይ በተፈጸመ በዚህ ጥቃት ቢያንስ ሁለት ፍንዳታዎች ተሰምተዋል።

ከፍንዳታው በኋላ በመስጊዱ በብዛት ለአርብ ስግደት የተገኙ ሰዎች ነፍሳቸውን ለማዳን በሩጫ ለመውጣት በሚሞክሩበት ጊዜ ውጪ ሆነው የሚጠብቁት ጥቃት ፈጻሚዎች ተኩስ ከፍተውባቸዋል።

ፍንዳታው በመስጊዱ ላይም ከፍተኛ ጉዳት እንዳደረሰም ዘገባዎች አመልክተዋል።

የግብጽ የጤና ጥበቃ ሚኒስትር ካሊድ ሙጃሂድ ለሀገሪቱ ቴሌቪዥን ሲናገሩ ጥቃቱን የሽብር ጥቃት ነው ብለውታል።

የሀገሪቱ ፕሬዝዳንት ከጥቃቱ በኋላ ከጸጥታ አማካሪዎቻቸው ጋር ስብሰባ የተቀመጡ ሲሆን የሶስት ቀናት ብሔራዊ ሀዘንም አውጀዋል።

እስካሁን ለጥቃቱ በይፋ ሃላፊነትን የወሰደ አካል ባይኖርም የግብጽ የጸጥታ ሃይሎች ግን በየቀኑ በሚባል ደረጃ ከአይሲስ ጋር ከወገኑ ሃይሎች ጥቃት እንደሚደርስባቸው ይነገራል።

ጥቃቱን ያደረሱት ሰዎችም ለጊዜው ወዴት እንደጠፉና በምን ሁኔታ ላይ እንዳሉ የታወቀ ነገር የለም።

የዛሬው ጥቃት ባሳይናይ ግዛት ከተፈጸሙት ጥቃቶች ሁሉ አስከፊው ነው ተብሏል።

ጥቃት ፈጻሚዎቹ በራት ተሽከርካሪዎች በመሆን ፍንዳታውን ካደረሱ በኋላ በአካባቢው ያሉ ተሽከርካሪዎችን በቦምብ በማጋየት ለአርብ ጸሎት በመስጊድ የተሰበሰቡትን ሰዎች ከአደጋው መውጫ አሳጥተዋቸዋል።

በግብጽ እንደ አውሮፓውያኑ አቆጣጠር በ2013 የሙስሊም ወንድማማቾች በመባል የሚታወቀው እንቅስቃሴ መሪ መሀመድ ሙርሲ ከስልጣን ከተወገዱ በኋላ የእስልምና አክራሪዎች ጥቃት በማድረስ ላይ ናቸው።

በ2014 ፕሬዝዳንት አልሲሲ በግዛቲቱ የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ ሲያውጁ አካባቢው የአሸባሪዎች መፈልፈያ ሆኗል ብለው ነበር።

በሳይናይ ግዛት ከ2014 ጀምሮ ለአይሲስ አጋርነታቸውን ከሚገልጹ ወገኖች በደረሰ ጥቃት በመቶዎች የሚቆጠሩ የጦር አባላትና ሲቪሎች ሕይወታቸውን አጥተዋል።