በጃፓን በጎርፍ አደጋ ቢያንስ መቶ ያህል ሰዎች ሞቱ

(ኢሳት ዲሲ–ሐምሌ 2/2010) በጃፓን ምዕራባዊ ክፍል የጣለው ከባድ ዝናብ ባስከተለው ጎርፍ ቢያንስ መቶ ያህል ሰዎች መሞታቸው ታወቀ።

ከተለመደው በሶስት እጥፍ በጨመረ መልኩ ጥሏል የተባለው ዝናብ ባስከተለው ጎርፍና የመሬት መደርመስ በርካታ የአካባቢው ነዋሪዎች የገቡበት አልታወቀም ተብሏል።

ከዚህ በፊት ታይቶ አይታወቅም የተባለው ይህ ዝናብ ባስከተለው አደጋም አካባቢው ከኤሌክትሪክ አገልግሎት ውጪ መሆኑ ታውቋል።

በአካባቢው ያለው ወንዝ በድንገት ሊገነፍል ይችላል በሚልም 2 ሚሊየን የሚሆኑ የአካባቢው ነዋሪዎች ከቀያቸው እንዲለቁ መደረጉም ታውቋል።

እንደ ቢቢሲ ዘገባ የአደጋ ጊዜ ሰራተኞች በፍርስራሹ ውስጥ የተቀበሩ ሰዎችን ለመታደግ የነፍስ አድን ስራ ላይ መሰማራታቸው ታውቋል።