በድሬዳዋ ሳተናው የተሰኘው ማህበር አመራሮችና አባላት ላይ እስራትና እንግልት እየተፈጸመባቸው ነው

(ኢሳት ዲሲ–ግንቦት 15/2011)በድሬዳዋ ያለውን ኢፍትሃዊነት ለመታገል በከተማዋ ወጣቶች የተቋቋመው ሳተናው የተሰኘው ማህበር አመራሮችና አባላት ላይ እስራትና እንግልት እየተፈጸመ መሆኑ ተገለጸ።

የማህበሩ ሊቀመንበር በፖሊስ ተይዞ ከታሰረ ወዲህ ቤተሰቦቹ እንዳይጠይቁት መደረጉን ነዋሪዎች ለኢሳት ገልጸዋል።

40 40 20 የተሰኘው የከተማዋ አስተዳደራዊ መዋቅር የድሬዳዋን ነዋሪዎች ባይተዋር ያደረገ ነው፡፡

መብታቸውን የገፈፈ ጨቋኝ መዋቅር ነው የሚል ተቃውሞ ይዞ የተነሳው የሳተናውን ማህበር ለማጥፋት የድሬዳዋ ከተማ አስተዳደር አፈና መጀመሩንም ገልጸዋል።

ሶስት የማህበሩ አመራሮችና አባላት በአሁኑ ሰዓት ያለምንም ክስ ከዚራ በሚገኝ ጨለማ እስር ቤት ውስጥ እየተሰቃዩ መሆናቸውን የደረሰን መረጃ አመልክቷል።

በጉዳዩ ላይ የድሬዳዋ ከተማ አስተዳደርና የፖሊስ ጽሕፈት ቤት ምላሽ እንዲሰጡን ያደረግነው ጥረት ለጊዜው አልተሳካም።