በውጭ የሚገኘው ሲኖዶስ በሙስሊሞች ላይ የተፈጸመውን ግድያ አወገዘ

ግንቦት ፬ (አራት) ቀን ፳፻፬ ዓ/ም

ኢሳት ዜና:-በስደት የሚገኘው የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቅዱስ ሲናዶስ፤  በአርሲ-አሰሳ የመብት ጥያቄ ባነሱ ሙስሊሞች ላይ የኢህአዴግ ታጣቂዎች  ተኩስ በመክፈት  የፈፀሙትን ግድያ አጥብቆ አወግዟል።

ሲኖዶሱ  በኢትዮጵያ ሙስሊሞች ላይ የተፈፀመውን ግድያ እና አሁንም እየተፈፀመ ያለውን  በደል ያወገዘው ሰሞኑን ያካሄደውን 33 ኛ ጉባኤውን ሲያጠናቅቅ ባወጣው የአቋም መግለጫ ነው።

ሲኖዶሱ በዚሁ የአቋም መግለጫው በአሰሳ-መስጊድ የተፈፀመውን ግድያ ከማውገዝ በተጨማሪ፤ ኢትዮጵያውያን ሙስሊሞች ህገ-መንግስቱ በፈቀደላቸው መሰረት  ሀይማኖታቸውን በነፃነት እንዳይከተሉ መንግስት ጣልቃ እየገባ በተለያዬ መንገድ ከሚያደርግባቸው ጫና በአስቸኳይ እንዲቆጠብ ጠይቋል።

ሀይማኖታዊ መብትን ከማስከበር እንቅስቃሴው ጋር ተያይዞ የታሰሩት ሙስሊም ወንድሞችና እህቶችም ፤ በቶሎ እንዲፈቱ ሲኖዶሱ አሣስቧል።

ክርስቲያኖች እና ሙስሊሞች ተዋደው እና ተከባብረው ከሚኖሩባቸው የዓለማችን አገሮች ኢትዮጵያ በግንባር ቀደምነት የምትጠቀስ እንደሆነች መረጃዎች ያሳያሉ።

ድምፃዊ ቴዎድሮስ ካሳሁን- በቅጽል ስሙ ቴዲ አፍሮ በምርጫ 97 ዋዜማ ባሰማው “ሸመንደፈር”የተሰኘ ሙዚቃው፦

“ሸገር አዲሳባ-አንች ያለሽበቱ፣

ራጉኤል አይደል ወይ-የአንዋር ጎረቤቱ፣

ቅዳሴ እና አዛኑን-አጥር ቢለያቸው፣

ፈጣሪ ከሰማይ-ባ’ንድነት ሰማቸው” በማለት፤ በኢትዮጵያ በሁለቱ እምነት ተከታዮች ዘንድ ያለውን ተከባብሮ እና ተዋዶ የመኖር ታሪክ እና እውነታ ይታወሳል።

ህዝባዊ ተቀባይነቱ በመሟጠጡ ከፍ ያለ ፖለቲካዊ ኪሳራ ውስጥ የሚገኘው ገዥው ፓርቲ፤ በተለይ ከቅርብ ዓመታት ወዲህ የሁለቱን እምነት ተከታዮች ለማጋጨት፣  በጥርጣሬ ለማስተያዬት እና በዚህም ህዝቡ በአገራዊ ጉዳዮች ላይ አንድ ላይ እንዳይቆም ለማድረግ በተደጋጋሚ አደገኛ ቅስቀሳዎችን ሲያደርግ መቆየቱን ብዙዎች ይናገራሉ።

በቅርቡ ብዙሀን ኢትዮጵያውያን ሙስሊሞች መብታቸውን ለማስከበር እንቅስቃሴ መጀመራቸውን ተከትሎ ፦አንድ ጊዜ “አክራሪዎችና አሸባሪዎች እየተስፋፉ ነው”  በማለት የነዛው ፕሮፓጋንዳ ህዝባዊ ተቀባይነት ሊያገኝለት እንዳልቻለ የተገነዘበው ኢህአዴግ፤ ከሰሞኑ ደግሞ ተቃውሞ ያሰሙትን ሙስሊሞች፦ “ሀሳባቸው የሸሪአ መንግስት ለማቋቋም ነው”በማለት በሌሎች እምነት ተከታዮች ዘንድ በጥርጣሬና በፍርሀት እንዲታዩ ቅስቀሳ መጀመሩ ይታወቃል።

የብዙሀኑ ሙስሊም አስተባባሪ ኮሚቴ ፦”በሀሰት ፕሮፓጋንዳ የመብት ጥያቄን ማዳፈን አይቻልም” በሚል ርዕስ ሰሞኑን  በበተነው ወረቀት ፤ መንግስት የዚህ ዓይነት ቅስቀሳ የጀመረው ፤የሙስሊሞች መብት የማስከበር እንቅስቃሴ በክርስቲያን ወንድሞቻቸው ዘንድ በጥርጣሬ እንዲታይና ድጋፍ እንዳያገኝ ለማድረግ መሆኑን በመጥቀስ፤ ከዚህ አይነት አደገኛ የውሸት ቅስቀሳ እንዲቆጠብ ማሣሰቡ አይዘነጋም።

የብዙሀኑን ሙስሊም አስተባባሪ ኮሚቴ እና በስደት የሚገኘው ሲኖዶስ ያወጧቸውን መግለጫዎች የተመለከቱ አንድ አባት፦” በሁለቱም ወገን የወጡት መግለጫዎች ፤መንግስት ተከባብረውና ተዋደው የኖሩትን ህዝቦች በእምነት ምክንያት ለማናቆር እና ለማጋጨት ለዓመታት ቢደክምም፤ኢትዮጵያውያን ሙስሊሞች እና ክርስቲያኖች  አንድኛቸው ለሌላው ያላቸው አክብሮት እና አስተሣሰብ ዛሬም እንደ ጥንቱ በፍቅር ላይ የተመሰረተ እንደሆነ  የሚያመለክቱ ናቸው”ብለዋል።

___________________________________________________________________________________________________________________________________________________

ESAT is the first independent Ethiopian satellite service tasked to produce accurate and balanced news and information, as well as other entertainment, sports and cultural programming created for and by Ethiopians.

ESAT is committed to the highest standards of broadcast journalism and programming and will strive to provide an outlet of expression to all segments of the diverse Ethiopian community worldwide