በኢትዮጵያ የተከሰተው የኑሮ ውድነት ህዝቡን እያማረረ መሆኑ ተሰማ።

(ኢሳት ዜና–ጥቅምት 24/2010) በኢትዮጵያ የተከሰተው የኑሮ ውድነት ህዝቡን እያማረረ መሆኑ ተሰማ።

ኢሳት ወደ ተለያዩ የኢትዮጵያ አካባቢዎች በመደወል ያነጋገራቸው ኢትዮጵያውያን እንደሚሉት የኑሮ ውድነቱ የመኖር ህልውናቸውን አደጋ ውስጥ ከቶታል።

በተለይ በዝቅተኛ የኑሮ ደረጃ ላይ የሚገኙ ኢትዮጵያውያን የዕለት ጉርሳቸውን መሸመት አቅቷቸው አደጋ ውስጥ መውደቃቸውን ነው የተናገሩት።

በሌላ ዜና በሀዋሳ ነጋዴዎችና ባለሀብቶች ምሬት ላይ መሆናቸው ተሰምቷል።

ከዋጋ ግሽበትና ከብር የመግዛት አቅም መቀነስ ጋር በተያያዘ ነጋዴው ለከፍተኛ ኪሳራ በተዳረገበት በዚህን ወቅት ለአባይ ቦንድ አዲስ ዙር ገንዘብ አምጡ በሚል በመንግስት በኩል ጫና እየተደረገባቸው መሆኑን የደረሰን መረጃ አመልክቷል።

የኑሮ ውድነቱ ከምን ጊዜው በላይ እየከፋ በመምጣቱ የሀገር ውስጥ ስደት መጨመሩን መረጃዎች ያሳያሉ።

የምግብ ሸቀጦች ዋጋ በሶስትና ከዚያ በላይ እጥፍ በመጨመሩ ህዝቡ መኖር እንዳቃተው እየገለጸ ነው።
መሰረታዊ የሆኑ የምግብ ሸቀጦች ዋጋቸው ከመጨመሩም በላይ አንዳንዶቹ ከገበያ ውስጥ በቀላሉ የማይገኙ በመሆናቸው ከፍተኛ አደጋ ውስጥ መግባታቸውን ያነጋገርናቸው ገልጸዋል።

በተለይም ጤፍ፣ ስኳር፣ ቲማቲምና ዘይት ላይ የተከሰተው የዋጋ ጭማሪ ህዝቡ ሊቋቋመው ከሚችለው በላይ በመሆኑ በቀን አንድ ጊዜ መብላት የማይችለው ኢትዮጵያዊ ቁጥር በከፍተኛ መጠን እየጨመረ መምጣቱንም መረጃዎች ይጠቁማሉ።

በተለይ በዝቅተኛ የኑሮ ደረጃ ላይ የሚገኙ ኢትዮጵያውያን የዕለት ጉርሳቸውን መሸመት አቅቷቸው አደጋ ውስጥ መውደቃቸውን ነው የተናገሩት።

ለሕጻናት የእለት ተእለት ምግብ የሆነውን ወተት እንኳን መስጠት ብርቅ የሆነበት ደረጃ ላይ መደረሱን ነው ነዋሪዎቹ በምሬት የሚገልጹት።

በሌላ በኩል የአባይ ዋንጮ በዙር ሀዋሳ መግባቱን ተከትሎ ነጋዴዎችና ባለሀብቶች ከፍተኛ መጠን ያለው ገንዘብ እንዲያዋጡ መወሰኑ ታውቋል።

የኢሳት ምንጮት እንደገለጹት የሀዋሳ ነጋዴዎች በተደራራቢ ጫናዎች መስራት ከማይችሉበት ደረጃ ላይ ናቸው።

በቅርቡ የተጣለባቸው ከአቅም በላይ ግብር በርካታ ነጋዴዎች ለኪሳራ ከመዳረጉም በላይ ጥቂት የማይባሉት ፍቃዳቸውን መመለሳቸውን ለማወቅ ተችሏል።

በየጊዜው እየጨመረ የመጣው የዋጋ ግሽበትም በሀዋሳ ነጋዴዎች ላይ ያመጣው ጉዳት ቀላል የማይባል ሲሆን በተያዘው ወር መጀመሪያ ላይ በመንግስት ርምጃ የተቀነሰው የብር የመግዛት አቅምም ለነጋዴው ብርቱ አደጋ ማምጣቱ ይነገራል።

በእነዚህ ምክንያቶች ለኪሳራ ተዳርጎ ከጨዋታ ውጪ በሆነው የሀዋሳ ነጋዴ ማህበረሰብ ላይ ለአባይ ግድብ ገንዘብ እንዲያዋጡ መገደዱ ከፍተኛ ምሬት ማስከተሉን ከምንጮቹ መረጃ ለመረዳት ተችሏል።

በዙር ሀዋሳ የደረሰው የአባይ ዋንጫ በየአከባቢው ህዝቡን ለስገዳጅ መዋጮ በመዳረግ እያማረረ መሆኑን የገለጹት ምንጮች በቅርቡ በሲዳማ ዞን በጭኮ መምህራን አናዋጣም በማለት የስራ ማቆም አድማ ማድረጋቸው የሚታወስ ነው።

አንዳንድ ነጋዴዎች እንደሚሉት ስራ በጠፋበት፣ ኢኮኖሚው በወደቀበት፣ ግብር ያለአቅም ተቆልሎ ነጋዴው ሀገር ጥሎ ለመሰደድ በቋፍ ላይ ባለበት በዚህን ወቅት ከፍተኛ መጠን ያለው ገንዘብ ለአባይ መዋጮ እንዲያቀርቡ በመንግስት ታዟል።

ከዚህ ቀደም በተደጋጋሚ ያዋጡት ገንዘብ ሳይመለስላቸው ሌላ ዙር መምጣቱ ግራ እንዳጋባቸውም ተናግረዋል።

የአባይ ግድብ በገንዘብ እጥረት ስራው ከቆመ ወራት የተቆጠሩ ሲሆን የአባይ ዋንጫ በየክልሉ እየዞረ ከፍተኛ መጠን ያለው ገንዘብ እንዲሰበሰብ ከአባይ ግድብ ብሄራዊ ምክር ቤት በተወሰነው መሰረት ህዝቡን ለምሬት የዳረገ መዋጮ በአስገዳጅነት እየተከናወነ ይገኛል።