በኢትዮጵያ ከግማሽ ሚሊዮን በላይ ጎዳና ተዳዳሪዎች አሉ

ህዳር ፲፰ (አስራ ስምንት) ቀን ፳፻፭  ዓ/ም

ኢሳት ዜና:-በአዲስ አበባ ከተማ ከአንድ መቶ ሺህ በላይ ጎዳና ተዳዳሪዎች መኖራቸውን የተባበሩት መንግስታት የህጻናት መርጃ ድርጅት ጥናት አመለከተ።

የኢትዮጵያ መንግስት ማእከላዊ ስታትስቲክ መስሪያ ቤት ደግሞ በአዲስ አበባ ያሉት ጎዳና ተዳዳሪዎች 60 000 ብቻ ናቸው የሚል መረጃ አሰራጭቷል።

የተባበሩት መንግስታት የአለም አቀፉ የህጻናት መርጃ ድርጅት ዩኒሴፍ እንዳመለከተው በኢትዩኦጵያ በአጠቃላይ ከግማሽ ሚሊዮን በላይ ጎዳና ተዳዳሪዎች ሲኖሩ ከዚህ ውስጥ አንድ መቶ ሺዎቹ በርዕሰ መዲናዋ አዲስ አበባ ይገኛሉ።

የኢትዮጵያ ማእከላዊ ስታትስቲክ መስሪያ ቤት በአጠቃላይ በኢትዮጵያ የሚገኙ ጎዳና ተዳዳሪዎች 150 000 ብቻ ናቸው ሲል አመልክቷል። ከዚህ ውስጥ አንድ ሶስተኛው ወይንም 60 000 ሺዎቹ በአዲስ አበባ ይገኛሉ ብሎል።

አለም አቀፍ ተቋማት የሚያወጡትን መረጃ የኢትዮጵያ መንግስት የማይቀበልባቸው አጋጣሚዎች የበዙ ናቸው። የአለም ጤና ድርጅት ከአለም ባንክ ጋር በጋራ ባወጡት ሪፖርት ከኢትዮጵያ ህዝብ ውስጥ 17.6 በመቶ ወይም 14 ሚሊዮን ህዝብ የአካል ጉዳተኛ ነው ማለታቸው ሲታወስ አዲሱ ጠቅላይ ሚኒስትር ሀ/ማሪያም ደሳለኝ ሳይንሳዊ በሆነ መንገድ አልተጠናም በማለት መቃወማቸው ተዘግቧል።