በኢትዮጵያ አየር መንገድ ላይ ያልተጠበቀ አደጋ ሊደርስ እንደሚችል ሰራተኞች አስጠነቀቁ

ሚያዚያ ፳፱ (ሃያ ዘጠኝ) ቀን ፳፻፬ ዓ/ም  

ኢሳት ዜና:-የኢትዮጵያ አየር መንገድ ባለፉት ሳምንታት ሸኚዎች ወደ ውስጥ ገብተው ዘመዶቻቸውን እንዳይሸኙ ክልከላ መጣሉን በተደጋጋሚ ስንዘግብ ቆይተናል። የአየር  መንገድ ሰራተኞች እንደሚሉት መንግስት እግዱን የጣለው የሽብር ጥቃት እንደሚፈጸም መረጃው ስለደረሰው ነው። ይሁን እንጅ አንዳንድ ወገኖች መንግስት ወደ ሳውዳ አረብያ  የሚጎርፉትን ወጣት ሴቶች ህዝቡ እንዳያያቸው የተጠቀመበት ስልት ነው ሲሉ በብዙ መቶዎች የሚቆጠሩ ወጣት ሴቶች በቦሌ አየር ማረፊያ ሲስተናገዱ በፊልም የተደገፈ መረጃ አቅርበዋል። ኢሳት ከአንዳንድ ሰራተኞች ባገኘው ጥቆማ መንግስት በሙስሊም ኢትዮጵያውያን የተነሳውን ተቃውሞ ለማብረድ እንዲሁም የምእርባዊያንን ድጋፍ እንደያዘ ለመቆየት ምናልባትም የተቀናበረ የፈጠራ የሽብር ጥቃት ራሱ አዘጋጅቶ ራሱ ሊፈጽም ይችላል የሚል ዘገባ ማቅረቡ ይታወሳል።

ዘገባው ከተላለፈ በሁዋላ ከፍተኛ የአየር መንገዱ ኢንጂነሮች መንግስት እያቀደ ካለው ድርጊት እንዲቆጠብ እና ህዝቡ ጥንቃቄ እንዲያደርግ በሚል ሚስጢራዊ መረጃዎችን ለኢሳት ልከዋል። እንደ ከፍተኛ ኢንጂነሮች ጥቆማ በቅርቡ የኢትዮጵያ አየር መንገድ ላለፉት 21 አመታት አገልግሎት ላይ የዋለውን ቦይንግ 757 – 260 ETAKC አስመስሎ በተሰራ የበረራ ክንፍ በማደስ 100 በመቶ የብቃት ደረጃውን ከፍ ለማድረግ ተችሎአል። በዚህም መሰረት በቦይንግ 757- 260 ET AKE ላይ ተመሳሳይ ስራ ይሰራል ተብሎ በእቅድ ተይዞ የነበረ ቢሆንም  ላለፉት 2 ወራት  ስራው ሳይጀመር ቆይቷል።

ሰሞኑን የስራ አመራር ሃላፊዎች በጣም ለተወሰኑ ቴክኒሻኖች በዚሁ አውሮፕላን ላይ ያሉ እጅግ ጠቃሚ የሆኑ እቃዎች በሚስጢር ከአውሮፕላኑ ላይ እንዲነሱ ጥብቅ በሆነ  ትእዛዝ ሰጥተዋል። ማኔጂመንቱ ለኢንጂነሮች  የሰጠው ምክንያት አውሮፕላኑ የሽብርተኝነት አደጋ ሊፈጸምበት እንደሚችል መረጃ ደርሶናል የሚል ነው። ኢንጂነሮች በበኩላቸው አውሮፕላኑ የሽብር ጥቃት የሚፈጸምበት ከሆነ በሚቀጥለው ሳምንት ስራ እንዲጀምር  ለማድረግ ለምን  ተፈለገ በማለት ይጠይቃሉ። ኢንጂነሮች እንደሚጠረጥሩት መንግስት በዚያ አውሮፕላን ላይ አንድ የሆነ አደጋ ሊፈጽም ተዘጋጅቷል ። ይሀው የበረራ መርሀ ግብሩን  አያይዘው የላኩት የአየር መንገዱ ከፍተኛ ኢንጂነሮች መረጃውን ይፋ ለማውጣት የፈለጉበትን መንገድም ገልጠዋል- ጉዳዩን ለህዝቡ አስቀድሞ በማሳወቅ መንግስት ነገሩ እንደ ታወቀበት አውቆ ከዚህ ድርጊቱ ይቆጠባል የሚል እምነት አለን በማለት ለኢሳት ገልጠዋል።

ጉዳዩን በማስመልከት የኢትዮጵያን አየር መንገድ ባለስልጣናት ለማነጋገር ብንሞክርም ሊሳካልን አልቻለም ይሁን እንጅ  አየር መንገዱ አስተያየቱን በማንኛውም ጊዜ ካቀረበ ለማውጣት ዝግጁ ነን። አንጋፋው የኢትዮጵያ አየር መንገድ በአቶ ግርማ ዋቄ አመራር በአፍሪካ ደረጃ ተመራጭ አየር መንገድ ለመሆን መብቃቱ ይታወሳል። አቶ ግርማ ዋቄ በጡረታ እንደተሰናበቱ  አቶ ተወልደ ገብረማርያምን የማኔጅመንቱን ስፍራ የተረከቡ ሲሆን ቀድሞ የቦርዱ ሊቀመንበር የነበሩት አቶ ስዩም መስፍን ደግሞ ስልጣኑን ለአቶ አዲሱ ለገሰ አስረክበዋል።

___________________________________________________________________________________________________________________________________________________

ESAT is the first independent Ethiopian satellite service tasked to produce accurate and balanced news and information, as well as other entertainment, sports and cultural programming created for and by Ethiopians.

ESAT is committed to the highest standards of broadcast journalism and programming and will strive to provide an outlet of expression to all segments of the diverse Ethiopian community worldwide