በአፋር አንድ ወጣት ተገደለ ሶስት ቆሰሉ

ሚያዚያ ፲፱ (አስራ ዘጠኝ) ቀን ፳፻፬ ዓ/ም  

ኢሳት ዜና:-በአፋር ክልል በዱብቲ ከተማ በህዝቡ እና በመንግስት ማካከል የተፈጠረው አለመግባባት ወደ ደም መፋሰስ እያመራ መሆኑን በተደጋጋሚ መዘገባችን የሚታወስ ሲሆን፣ በዛሬው እለት የፌደራል ፖሊስ አባላት የ17 አመቱን የ7ኛ ክፍል ተማሪ የሆነውን አሊ ኡመር ሙሀመድን በሶስት ጥይት ገድለው በጓደኞቹ ላይ ደግሞ ከፍተኛ የሆነ ድ ብደባ ፈጽመዋል።

የአካባቢው ነዋሪዎች እና የቀበሌ አመራሮች ሳይቀሩ የልዩ ሀይል የፌደራል ፖሊስ አባላትን ልትጨርሱን ነው ወደ ዚህ የመጣችሁት በማለት ሲቃወሙዋቸው ነበር። ሟቹን ለመቅበር በጸሎት ላይ የነበሩ ሰዎችን የኢሳት ዘጋቢ ባነጋገረበት ወቅት ከፍተኛ የሆነ ቁጣ እና ብስጭት በህዝቡ ዘንድ ይሰማ ነበር። አንድ ስማቸው እንዳይገለጥ የፈለጉ ሰው እንደተናገሩት ህዝቡ የሟቹን ደም ለመበቀል ከየአካባቢው እየተሰባሰበ መሆኑን ከዚህ በሁዋላ የሚፈጠረውን ነገር ለመገመት እንደማይችሉ ገልጠዋል

በቀብሩ ስነስርአት ላይ የነበሩ አንድ የቀበሌ ታጣቂ እንደገለጡት የወጣቱን ሞት ተከትሎ የክልሉ ባለስልጣናት በአካባቢው ተገኝተዋል፤ ይሁን እንጅ ህዝቡ አትወክሉንም ብሎአቸዋል።

በጉዳዩ ዙሪያ የአፋር ሰብአዊ መብቶች ድርጅት ሀላፊ የሆኑትን አቶ ገአስ አህመድን ስለጉዳዩ አነጋግረናቸዋል።

የመለስ መንግስት ከቅርብ ጊዜ ወዲህ በመላው አገሪቱ መለስ ቀለስ የሚል ተቃውሞ እየገጠመው ነው። እስካሁን ድረስ ተቃውሞዎችን  ሁሉ በሀይል ለመጨፍለቅ የሚያደርገው ሙከራ አገዛዙን ከህዝብ እየነጠለውና መተማመኛውን በወታደሩ ላይ እንዲያደርግ እንዳስገደደው ተንታኞች ይናገራሉ። በአሁኑ ጊዜ በመላ አገሪቱ የሚሰሙት የተቃውሞ ድምጾች እየጎሉ መምጣት፣ ለአገዛዙ ትልቅ ራስ ምታት ሆነዋል። በአለፉት ሁለት ሳምንታት ብቻ በጋምቤላ በአስራዎች የሚቆጠሩና በጎፋ ዞን 5 ሰዎች በፌደራል ፖሊስ አባላት ተገድለዋል።

___________________________________________________________________________________________________________________________________________________

ESAT is the first independent Ethiopian satellite service tasked to produce accurate and balanced news and information, as well as other entertainment, sports and cultural programming created for and by Ethiopians.

ESAT is committed to the highest standards of broadcast journalism and programming and will strive to provide an outlet of expression to all segments of the diverse Ethiopian community worldwide