በአፋር በተነሳ ተቃውሞ ከ100 በላይ ሰዎች ታሰሩ

(ኢሳት ዲሲ–ሚያዚያ 11/2011) በአፋር ክልል በዞን አምስት ገለአሉ ሶምሮቢ በሚባል ወረዳ በተነሳ ተቃውሞ ከ100 በላይ ሰዎች መታሰራቸው ተገለጸ።

ፋይል

የአፋር የሰብዓዊ መብቶች ድርጅት ለኢሳት እንደገለጸው በክልሉ የተንሰራፋውን ጎሰኝነት በመቃወም ካለፈው ሳምንት ጀምሮ እየተካሄደ ያለውን ተቃውሞ ለማስቆም የአፋር ልዩ ሃይል ደብደባና እስር በመፈጸም ላይ ነው።

ለውጥ አፋር ላይ አልመጣም፣ ማሻሻያው ይበልጥ ጎሰኝነትን አስፋፍቷል በሚል የተነሳው ተቃውሞ ወደሌሎች አካባቢዎችም መዛመቱን ለማወቅ ተችሏል።

የአፋር ወጣቶች ስብስብ ዲኮኢና የፌደራል መንግስት አፋጣኝ መፍትሄ እንዲሰጥ በመጠየቅ መግለጫ አውጥቷል።

የአፋር የሰብዓዊ መብት ድርጅት በአፋር እየተካሄደ ያለውን የሰብዓዊ መብት ጥሰት በተመለከተ ጄኔቫ ለሚገኘው የተባበሩት መንግስታት ድርጅት የሰብዓዊ መብት ጉዳይ ጽሕፈት ቤት ማሳወቁን ገልጿል።