በአድዋ ከተማ አደባባይ ላይ ተሰቅሎ የነበረ የ አቶ መለስ ፎቶ ተቀዳዶ ተጣለ-የራስ አሉላ አባ ነጋ ት/ቤት ስያሜ በአቶ መለስ ስም ተቀየረ

ህዳር ፲፰ (አስራ ስምንት) ቀን ፳፻፭  ዓ/ም

ኢሳት ዜና:-በትግራይ ክልል  በአድዋ ከተማ አደባባይ ላይ ተሰቅሎ የነበረ የአቶ መለስ  ዜናዊ ፖስተር ተቀዳዶ ተጣለ

ኢየሩሳሌም አርአያ ምንጮቹን ጠቅሶ እንደዘገበው በሁኔታው የተበሳጩት የክልሉ ካድሬዎች ለተፈ}መው ድርጊት ጣታቸውን ወደ አረና ለትግራይ ፓርቲ ቀስረዋል።

የህወሀት ካድሬዎቹ፦« የመድረክ ተለጣፊ የሆነው አረና ፓርቲ ነው ይህን የፈፀመው » በማለት ያልተጨበጠ የፈጠራ ወሬ እያሰራጩና በድርጅቱ ላይ  እየዛቱ ነው።

የዜናው ምንጮች  ግን ፦”ድርጊቱን የፈፀመው የአካባቢው ህዝብ እንጂ የትኛውም ተቃዋሚ ፓርቲ አይደለም”ሲሉ  ተናግረዋል።

አድዋ የ አቶ መለስ ዜናዊ የትውልድ ከተማ መሆኑ ይታወቃል።

ይህ በ እንዲህ እንዳለ በትግራይ ተምቤን – አብዪአዲ  ውስጥ የሚገኘውና በጀግናው ራስ አሉላ አባነጋ ስም ተሰይሞ የቆየው የሁለተኛ ደረጃ ት/ቤት ስሙ ተቀይሮ በመለስ ዜናዊ ስም እንዲሰየም መወሰኑን  ምንጮቹ አክለው ገልጸዋል።

በደርግ ዘመን የተሰራውና በራስ አሉላ ስም ተሰይሞ  የ9ኛ እና የ 10ኛ ክፍል ተማሪዎችን ተቀብሎ ሲያስተምር የቆየው ይኸው ትምህርት ቤት፤ ከ2002 ዓ.ም ጀምሮ በአገር ውስጥና በውጭ አገራት የሚገኙ የአካባቢው ተወላጆች ባዋጡት ገንዘብ   እስከ 12ኛ ክፍል ተማሪዎችን ማስተናገድ እንዲችል የማስፋፊያና  አቅም የማሳደግ  ሥራ  ተከናውኖለታል።

የትምህርት ቤቱ የማስፋፊያ ግንባታ ተጠናቆ ባለፈው ነሃሴ ወር ሊመረቅ በዝግጅት ላይ እንዳለ አቶ መለስ በማለፋቸው ፕሮግራሙ መሰረዙ የታወቀ ሲሆን፤ የክልሉ ከፍተኛ ባለስልጣናት በስፍራው በተገኙበት  ከሁለት ሳምንት በፊት ተመርቋል።

በምረቃው ሥነ-ስርዓት ላይ  የራስ አሉላ ስም ተሰርዞ « መለስ ሁለተኛ ደረጃ ት/ቤት » ተብሎ መሰየሙን ባለስልጣናቱ በይፋ ተናግረዋል።

በት/ቤቱ በይፋ የመለስ ስም ተፅፎ መለጠፉ  የገለጹት የዜናው ምንጮች፤ በህዝብ ገንዘብ መዋጮ የተገነባን ት/ቤት  ስያሜ መለወጥ፤በጡንቻና በማን አለብኝነት ህዝብን የመናቅ  ተግባር ነው ሲሉ የአካባቢው ተወላጆች ማውገዛቸውን ተናግረዋል።

በተለይ በአውስትራሊያ፣ በጀርመን፣ በኖርዌይ፣ በአሜሪካ፣ በካናዳና… ሌሎች አገራት የሚኖሩ የአካባቢው ተወላጆች ባካሄዱት ቴሌ ኮንፈረንስ ከፍተኛ ተቃውሞ አሰምተዋል።

ተሳታፊዎቹ ፦ « የአፄ ምንሊክንና የሰማዕቱ አቡነ ጴጥሮስን ሃውልት ለማፍረስ የተጀመረው አፍራሽ እንቅስቃሴ ወደ ራስ አሉላ ተሻግሯል። ይህ የሚያመለክተው  ሰዎቹ የቆየውን የኢትዮጵያን ታሪክ ለማጥፋት ቆርጠው መነሳታቸውን ነው። ይህ ትውልድ ታሪኩን አስጠብቆ የማቆየት፤ የተጀመረውን አደገኛ አፍራሽ እንቅስቃሴ ከማውገዝ ባለፈ ለትግል መነሳሳት አለበት።ኢትዮጵያዊያን እጅ ለእጅ መያያዝ አለብን፤» ነው ያሉት።

አንድ የውይይቱ ተሳታፊ፦« የኢትዮጵያዊነት ጉልህ መታወቂያና መገለጫ የሆኑ አኩሪ ታሪኰችንና ታሪክ ሰሪ ጀግኖችን ለማጥፋት  ቴዎድሮስ ሃጎስ፡ በረከት ስሞዖንና ስብሃት ነጋ የሚመሩት አካል በአገራችን ላይ የጥፋት ዘመቻ ከፍተዋል» ሲሉ ተናግረዋል።

ቀደም ሲል  « የዶጋሊ ዘመቻ » እየተባለ በየአመቱ ራስ አሉላ የሚዘከሩበት ታሪካዊ ቀን እንደነበረ እና ሕወሓት ወደ ስልጣን ከመጣ በሑዋላ ግን ይህ በዓል  እንዲቀር መደረጉን እነዚሁ ወገኖች ያስታውሳሉ።

በሌላም በኩል በመቀሌ ከተማ ፒያሳ አካባቢ የአፄ ዮሃንስን መታሰቢያ ሃውልት ለማቆም ተጀምሮ የነበረው እንቀስቃሴ እንዲቆም መደረጉን የቅርብ ምንጮች አጋልጠዋል።  ሐውልቱ እንዳይሠራ የተወሰነው ባለፈው አመት ከህዝብ በተዋጣ ገንዘብ ሓውልቱን ለማቆም የመሰረት ድንጋይ ከተጣለ በሁዋላ እንደሆነ ተገልጿል።