በአዲስ አበባ እና በአርባምንጭ ከተሞች በቡራዩና ዙሪያ ከተሞች የተፈጸሙትን ግድያዎች የሚያወግዙ የተቃውሞ ሰልፎች ተካሄዱ

በአዲስ አበባ እና በአርባምንጭ ከተሞች በቡራዩና ዙሪያ ከተሞች የተፈጸሙትን ግድያዎች የሚያወግዙ የተቃውሞ ሰልፎች ተካሄዱ
( ኢሳት ዜና መስከረም 07 ቀን 2011 ዓ/ም ) በአዲስ አበባ የመከላከያ ሰራዊት አባላት በሰልፈኛው ላይ በወሰዱት እርምጃ እስካሁን 5 ሰዎች መገደላቸውን የደረሱን መረጃዎች ያመለክታሉ። በቡራዩና በተለያዩ የአዲስ አበባ ዙሪያ ከተሞች የተደራጁ ወጣቶች በፈጸሙት ጥቃት በርካታ ዜጎች ተገድለዋል። በሺዎች የሚቆጠሩ ዜጎችም ተፈናቅለዋል። መንግስት ወንጀለኞችን በቁጥጥር ስር ማዋሉንና አስፈላጊውን እርምጃ እንደሚወስድ ተናግሯል። ህዝቡ ግን መንግስት እየወሰደ ያለው እርምጃ በቂ አይደለም፣ ወንጀለኞችን ማባበል ይዟል የሚል ትችት እያቀረበ ነው። አዲስ አበባ የሚገኘው የኢሳት ሪፖርተር ጋዜጠኛ ስለሺ ሽብሩ የህዝቡ ስሜት ምን ይመስል እንደነበር ጥያቄ አቅርበንለታል።
የፖሊስ ኮሚሽነር ዘይኑ ጀማል ቡራዩ አካባቢ ብዙ ሰዎች መገደላቸውንና የብሄር ጥቃት ለመፈጸም መሞከሩን ተናግረዋል። ይህን ደግሞ ከጀርባ ሆነው የመሩ ሰዎች መኖራቸውንና ብዙዎችን በቁጥጥር ስር ማዋላቸውን ገልጸዋል። የጦር መሳሪያ ሊቀሙ የሞከሩ 5 ሰዎች መገደላቸውንና በርካቶች መቁሰላቸውን ኮሚሽነሩ ተናግረዋል።
በጦር ሃይሎች አካባቢ የነበረ አንድ የአይን እማኝ ግን ሰዎቹ የተገደሉት በቁጥጥር ስር ከዋሉ በሁዋላ ነው በማለት የፖሊስን መረጃ የሚቃረን መረጃ ለኢሳት ሰጥቷል።
በቡራዩ አካባቢ ተገኝቶ ሰዎችን ያነጋገረው ወጣት ሄኖክ እንዳለው፣ ጥቃቱን የሚፈጽሙት ቀደም ብለው በአካባቢው የነበሩና ሲደራጁ የነበሩ ሰዎች ናቸው ይላል።
በአርባምንጭም እንዲሁ ተመሳሳይ ተቃውሞ ሲካሄድ ውሎአል። መከላከያ ገብቶ ተቃውሞውን ለመቆጣጠር በርካታ ጥይቶች ተኩሷል። 8 ሰዎች ቆስለው ሆስፒታል የገቡ ሲሆን፣ አንደኛው ህይወቱ አልፏል። በአርባ ምንጭ የተካሄደውን የተቃውሞ ሰልፍ በጥርጣሬ የተመለከቱት ብዙዎች ናቸው። ሰልፉ ሆን ተብሎ በመስተዳድሩ ባለስልጣናት የተቀናበረና የብሄር ግጭት ለመፍጠር ያለመ እንደነበር ያነጋገርናቸው የከተማዋ ነዋሪዎች ይገልጻሉ። በቅርቡ ከእስር የተፈታው አቶ ሉሉ መሰለ መስተዳድሩ ስለፉን ከፈቀደ በሁዋላ ሃላፊነት የሚወሰድ ሰው ሳይመድብ እንዲካሄድ ማድረጉ ጥርጣሬ ላይ እንደከተተው ተናግሯል
ሌላው የከተማው ነዋሪም እንዲሁ በቡራዩ የተከሰተውን አጋጣሚ በመጠቅም ለውጡን የሚቃወሙ የመስተዳድሩ ባለስልጣናት ሰልፉን ወደ አልተፈለገ አቅጣጫ ሊወስዱት ፈልገው እንደነበር ይናገራሉ።