በትግራይ የተለያዩ ከተሞች ከመሃል አገር የሄዱ ሰራተኞች እየታሰሩ ነው ቤተሰቦቻቸው አድራሻዎቻቸውን ማወቅ አልቻንም ሲሉ ተናግረዋል።

(ኢሳት ሐምሌ 27/2010)በመቀሌ፣ ዓድዋ፣ አክሱምና አዲግራት አካባቢ ለስራ ጉዳይ ሲንቀሳቀሱ የነበሩ ሾፌሮችን፤ በተለያዩ የስራ ጉዳዮች ከመሃል አገር ለስራ የተሰማሩ ወጣቶችን ካለምንም የፍርድ ቤት ማዘዣ “ሰላዮች ናችሁ” በሚል እያሰሩ እንደሚገኙ ታውቋል።
ካለምንም ጥፋታቸው ከስራ ገበታቸው፣ ከመንገድ ላይ ታፍነው የተያዙት ዜጎችን አድራሻ የት እንደታሰሩና፤ በምን ዓይነት ሁኔታ ላይ እንደሚገኙ ማወቅ ባለመቻላቸው ቤተሰቦቻቸው ስጋት ላይ ወድቀዋል። ከህግ አግባብ ውጭ ታስረው አድራሻቸው የጠፉ ዜጎችን ፣ ሁኔታ አጣርቶ መንግስት እንዲያሳውቃቸው ቤተሰቦች እየተማጸኑ ነው።
ህዝቡ በስጋት ህወሃትን እንዲደግፍ የማድረግ ዘመቻው ተጠናክሮ የቀጠለ ሲሆን፣ በተለያዩ ክልሎች የሚኖሩ የትግራይ ተወላጆች ደግሞ ወደ ክልላቸው እንዲመለሱ እየተጠየቁ ነው። ከፌደራል መንግስት የተላኩ ኮማንዶዎች ትግራይ ገብተዋል በሚል ያልተጨበጠ ወሬ መቀሌ ውስጥ ፍተሻ መካሄዱንም ስማቸው እንዳይገለጽ የፈለጉ አንዳንድ ነዋሪዎች ለኢሳት ገልጸዋል።
ህወሃቶች በጠ/ሚኒስትር አብይ አህመድ ላይ የሚያካሄዱትን ዘመቻ አጠናክረው ቀጥለዋል። ህወሃት አሁን ባለው ቁመና በተለያዩ አካባቢዎች መጠነኛ ሰላም ለማደፍረስ የሚያስችል የገንዘብ እና የመሳሪያ አቅም ቢኖረውም፤ በፌደራል ደረጃ የቀድሞ ስልጣኑን መልሶ የሚይዘበት አቅም እንደሌለው ከኢህአዴግ አካባቢ የተገኙ መረጃዎች ያሳያሉ። ህወሃት የትግራይን ህዝብን ከጎኑ ለማሰለፍ ሲል የተለያዩ የሽብር ወሬዎችን እየነዛ ቢሆንም፣ አብዛኛው የትግራይ ህዝብ ለህወሃት ቅስቀሳ ጆሮ እንደማይሰጥና የለውጡ ደጋፊ እንደሆነ ያነጋገርናቸው ሰዎች ይገልጻሉ።