በተጠናቀቀው የስራ አስፈጻሚ ስብሰባ በአባይ ጸሃዬ የተማራው ህወሃት ከኦህዴድ ባለስልጣናት ጋር ጸብ ቀረሽ ክርክር ማድረጉ ታወቀ

በተጠናቀቀው የስራ አስፈጻሚ ስብሰባ በአባይ ጸሃዬ የተማራው ህወሃት ከኦህዴድ ባለስልጣናት ጋር ጸብ ቀረሽ ክርክር ማድረጉ ታወቀ
(ኢሳት ዜና ማጋቢት 14 ቀን 2010 ዓ/ም) የኢሳት ምንጮች እንደገለጹት ለሳምንት በተደገረው የስራ አስፈጻሚ ስብሰባ ህወሃት በአቶ አባይ ጸሃዬ ዋና ተከራካሪነት ተወክሏል። ከአቶ አባይ ጀርባ አቶ ስብሃት ነጋና አቶ በረከት ስምዖን ተሰልፈው በኦህዴድ ላይ ከፍተኛ ዘመቻ አድርገዋል። ኦህዴድ በአቶ ለማ መገርሳ ዋና ተከራካሪነት ሲቀርብ፣ ዶ/ር አብይ አህመድም ከአቶ ለማ ጀርባ ሆነው ክርክራቸውን አድርገዋል።
ህወሃት ኦህዴድን በጎራ መደባለቅና በህዝበኝነት እንዲሁም የኢህአዴግን መስመር በመሳት ሲገመግም፣ ኦህዴድ በበኩሉ የኢትዮጵያን ህዝብ ጥያቄ እስካሁን በተሄደበት መስመር መመለስ እንደማይቻል ተከራክሯል። የርእዮት ዓለም ክርክር በተካሄደበት ስብሰባ ላይ ኦህዴድና ህወሃት የተለያዩ አመለካከቶችን ማራመዳቸው ለነባሩ አመራሮች የሚዋጥ አልሆነም።
የጠ/ሚኒስትር ሹመት ሃሳብ በተነሳበት ወቅት፣ ህወሃት እንዲህ የተዛነፈና ከመስመር የወጣ ሃሳብ ለያዙ ቡድኖች የአገሪቱን አመራር መስጠት በድርጅቱም በአገሪቱም ላይ መቅሰፍት እንዲመጣ መጋበዝ ነው ሲል፣ ኦህዴድ በበኩሉ ለህዝብ ጥያቄ ቅድሚያ በመስጠት ድርጅቱንም አገሪቱንም ከችግር የሚያወጣት መሪ ሊመረጥ ይገበዋል የሚል አቋም አራምዷል።
ለጠ/ሚኒስትር እጩ ሆነው ስለቀረቡት ሰዎች ግምገማ በሚካሄድበት ወቅት፣ በዶ/ር አብይ ላይ ዋና ተቺ ሆነው የቀረቡት አቶ አባይ፣ አቶ ስብሃትና አቶ በረከት ናቸው። የዶ/ር አብይ ዋና ደጋፊ ሆነው የተካራከሩት ደግሞ አቶ ለማ ናቸው። በአቶ ለማና በአቶ አባይ መካከል የተካሄደው ክርክር አቶ አባይ የሃይላንድ ውሃቸውን እስከመወርወር አስደርሷቸው እንደነበር የገለጹት ምንጮች፣ ክርክሩ መቋጫ እንደማይኖረው ሲታይ፣ ህወሃት ኦህዴድ ያቀረበውን እጩ እንደሚቀበል ነገር ግን መከላከያና ደህንነቱን በጠ/ሚኒስትሩ እዝ ስር ማድረጉን እንደሚቃወም አስታውቋል። ህወሃት መከላከያው በዶ/ር ደብረጺዮን እጅ እንዲሆን እና በጠ/ሚኒስትሩና በመከላከያ አዛዡ መካከል እኩል የስልጣን ክፍፍል እንዲኖር ሃሳብ አቅርቧል። ጠ/ሚኒስትሩ የአገሪቱን የደህንነት ተቋም ለመምራት ብቃት እንደሌለው በእነ አባይ በኩል የቀረበውን ሃሳብ፣ በቅድሚያ የተቃወሙት ዶ/ር አብይ ሲሆኑ፣ እርሳቸው የማንም ቧንቧ ለመሆን ፍላጎት የለኝም” በማለት መናገራቸውን ምንጮች አክለው ገልጸዋል።
ስብሰባው ያለ ስምምነት የተቋጨ መሆኑን በምክር ቤት ስብሰባ ወቅት እንዲቀጥል ተስማምተው መለያየታቸውን ምንጮች አክለው ገልጿል። ህወሃት የመከላከያ ስልጣኑን ለማንም አሳልፎ እንደማይሰጥ አቋሙን ግልጽ ያደረገ በመሆኑ፣ ይህን አቋሙን ካልቀየረ በምክር ቤት ስብሰባ ላይም መፍትሄ ይገኛል ብለው እንደማያስቡ ምንጮች አክለው ገልጸዋል።